Sunday, May 19, 2024
spot_img

በምዕራብ ኦሮሚያ የትራንስፖርት እንቅስቃሴ መስተጓጎሉ ተነገረ

አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ነሐሴ 8፣ 2013 ― በምዕራብ ኦሮሚያ በሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች ምክንያት የትራንፖርት እንቅስቃሴ መስተጓጎሉን ነዋሪዎች እና የአካባቢው አስተዳዳሪዎች ነግረውነናል ብሎ ቢቢሲ አስነብቧል፡፡መ

በቄለም ወለጋ እና በምዕራብ ወለጋ ዞኖች ውስጥ በሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች ምክንያት ዋና መንገዶች በመዘጋታቸው ከቦታ ቦታ ለመንቀሳቀስ መቸገራቸውን ነዋሪዎች ሲናገሩ፣ የአካባቢዎቹ ባለሥልጣናት ደግሞ ችግሩ የተፈጠረው በስጋት ምክንያት ነው ብለዋል።

እንደ አካባቢው ነዋሪዎች ከዚህ በፊት አጋጥሞ በማያውቅ ሁኔታ ከግምቢ ነጆ፣ ከግምቢ ደምቢ ዶሎ፣ ከጊዳሚ አሶሳ የሚወስዱ መንገዶች ተዘግተዋል፡፡

መንግሥት አሸባሪ ሲል የፈረጀው የሸኔ ጦር አዛዥ ኩምሳ ድሪባ ሰሞኑን ለቢቢሲ እንደተናገረው በምዕራብ ኦሮሚያ በርካታ የገጠር አካባቢ እና ትንንሽ ከተሞችን በእጃቸው ማስገባታቸውን መናገሩን ዘገባው አስታውሷል፡፡

የምዕራብ ወለጋ እና የቄለም ወለጋ ዞን አስተዳዳሪዎች በበኩላቸው የተዘጋ መንገድም ሆነ በአማጺያኑ ቁጥጥር ስር የገባ ስፍራ የለም ሲሉ አስተባብለዋል።

የሁለቱ ዞኖች አስተዳዳሪዎች የትራንስፖርት መስተጓጎል የተፈጠረው ታጣቂዎች በኃይል ከሾፌሮች ላይ ቁልፍ እየተቀበሉ ተሽከርካሪዎችን እየወሰዱ ስለሆነ ነው ብለዋል፡፡

የምዕራብ ወለጋ አስተዳዳሪ አቶ ኤልያስ ኡመታ ባለፉት ቀናት የሸኔ ታጣቂዎች ወደ ዋና መንገድ በመውጣት ከሾፌሮች ቁልፍ እየተቀበሉ መኪና ከቀሙ በኋላ ወደ ጫካ እየተመለሱ በመሆኑ በአንዳንድ አካባቢዎች የትራንስፖርት መስተጓጎሎች ተፈጠረ እንጂ መንገድ ሙሉ በሙሉ አልተዘጋም ብለዋል።

አስተዳዳሪው አክለውም፣ ኦነግ ሸኔ የሚሏቸው ታጣቂዎች ኋላ ቀር መሳሪያዎችን እንዲሁም ባዶ እጃቸውን በመሆን ሹፌሮችን በማስፈራራት ቁልፍ እየተቀበሉ እነደነበር ገልጸዋል።

በዚህ ሳምንት ውስጥ በቄለም እና በምዕራብ ወለጋ ዞኖች ውስጥ ከፍተኛ ወታደራዊ እንቅስቃሴ ሲካሄድ እንደነበር የአካባቢዎቹ ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡

የቄለም ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ገመቹ ጉርሜሳ በበኩላቸው ዞኑን አቋርጦ በሚያልፈው መንገድ፤ ትራንስፖርት የተስተጓጎበትን ምክንያት ሲያስረዱ “እነዚህ ታጣቂዎች ከሾፌሮች ቁልፍ እየተቀበሉ መኪኖችን እየወሰዱ ትራንስፖርት እንዲስተጓጎል ስላደረጉ እንጂ እንደ ከዚህ ቀደሙ መንገድ ተዘግቶ አይደለም” ብለዋል።

ከሁለት ቀናት በፊት በሃዋ ገላን ወረዳ በተለምዶ የሱሲ ተብሎ በሚጠራው ቦታ ታጣቂዎች ከሾፌሮች ቁልፍ በመንጠቅ ሦስት መኪኖችን እንደወሰዱ አቶ ገመቹ አረጋግጠዋል።

በዞኑ አንዳንድ ወረዳዎችም በድንጋይና በእንጨት መንገድ ለመዝጋት ተሞክሯል የሚሉት አስተዳዳሪው፣ ይህ ሙከራም በፍጥነት እንደከሸፈ እና በዚህ መልኩም የተዘጋ መንገድ እንደተከፈተም ገልጸዋል።

የምዕራብ ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ኤልያስ “በአሁኑ ወቅት የእነዚህን ታጣቂዎች እንቅስቃሴ ለማስቆም መፈተሽ ያለበት ስፍራ ተፍሾ፣ መታየት ያለበት ቦታ ታይቶ የኅብረተሰቡ እንቅሰቃሴ ወደ ቀድሞው ተመልሷል” ሲሉ ተናግረዋል።

ሆኖም ከነቀምት ባሕር ዳር ከሚወስደው መንገድ በስተቀር ሌሎቹ በእነዚህ ታጣቂዎች ቁጥጥር ስር መግባቱን ቢቢሲ ነዋሪዎች ነግረውናል ነው ያለው፡፡

የቄለም ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ገመቹ በበኩላቸው የእነዚህ ታጣቂዎች እንቅስቃሴ አልፎ አልፎ አንዳንድ ወረዳ ውስጥ ይታያል ግን ከመንግሥት አቅም በላይ የሆነ እንቅስቃሴ የለም ሲሉ ያስረዳሉ።

አቶ ገመቹ ‹‹ጦርነት የሚካሄድበት እና ገፍተው የሚወጡበት ስፍራን በሙሉ ተቆጣጥረናል ይላሉ እንጂ የተቆጣጠሩት አንድም ቀበሌ እና ወረዳ የለም። አይቻልምም›› ይላሉ፡፡

መንግሥት በሽብርተኛ ቡድንነት የፈረጃቸው ህወሓትና ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ብሎ የሚጠራው ቡድን ከኢትዮጵያ መንግሥት አንጻር በወታደራዊ መስክ ለመተባበር መስማማታቸውን ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img