Sunday, September 22, 2024
spot_img

በሶማሊ ክልል ለተከሰተው ድርቅ ዓለም አቀፍ ተቋማት አስቸኳይ የሰብአዊ ዕርዳታ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀረበ

አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ታኅሣሥ 7፣ 2014 ― በሶማሊ ክልል ለተከሰተው ድርቅ ዓለም አቀፍ ተቋማት አስቸኳይ የሰብአዊ ዕርዳታ እንዲያደርጉ ጥሪ ያቀረበው የሶማሊ ጉዳይ ኮንግረስ ነው፡፡

ኮንግረሱ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ባወጣው መግለጫ፣ በክልሉ በተደጋጋሚ ድርቅ መከሰቱ የማህበረሰቡን የመቋቋም አቅም በማሽቆልቆል ማህበረሰቡን ለከፋ አደጋ አጋልጦጣል ብሏል፡፡

ሆኖም ይህ ባለበት የክልሉ መንግስት ሰብአዊ እርዳታ ለተጎጂው ማህበረሰብ ከማድረስ ይልቅ የተመደበውን በጀት ለምርጫ ማስኬጃነት አውሎታል ሲል የወነጀለው ኮንግረሱ፣ የክልሉ ባለስልጣናትም ‹‹ህዝብ ለማዳን ተጨማሪ በጀት ከመመደብ ይልቅ ሐብት በማሸሽ ተግባር ላይ መጠመዳቸው›› እንደሚስተዋል አመልክቷል፡፡

በመሆኑም ዓለም አቀፍ ተቋማት የችግሩን አሳሳቢነት በመረዳት አስቸኳይ የሰብአዊ ዕርዳታ እንዲያደርጉ ጥሪውን አቅርቧል፡፡

በሶማሊ ክልል ዳዋ ዞን በተከሰተ ድርቅ 25 ሺሕ ገደማ የቁም እንስሳት መሞታቸውን የሶማሊ ክልል አደጋ መከላከል እና ዝግጁነት ቢሮ በቅርቡ ለመገናኛ ብዙኃን አስታውቋል፡፡

የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ሳዲቅ አብዱቃድር አስቸኳይ ድጋፍ ካልተገኘ አሁን ከሞቱት በላይ እንስሳት ሕይወት ሊያልፍ ይችላሉ ሲሉ አስጠንቅቀው ነበር፡፡

በክልሉ በአሁኑ ወቅት በአጠቃላይ ከ83 ሺሕ በላይ ነዋሪዎች አስቸኳይ የምግብ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የሚነገር ሲሆን፣ ከነዚህ ውስጥ ከተለያየ ቦታ ተፈናቅለው ካምፕ ውስጥ የሚገኙ ዜጎችት በቁጥር 33 ሺሕ ገደማ፣ እንዲሁም የዚያው የዳዋ ዞን ነዋሪዎች በቁጥር ከ50 ሺሕ በላይ ናቸው፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img