Sunday, October 6, 2024
spot_img

የሱዳን መፈንቅለ መንግስት የሲቪልና ወታደራዊ አመራሮችን እያካሰሰ ነው

አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ መስከረም 14፣ 2014 ― የነጻነት እና የለውጥ ሀይል ጥምረት በመባል የሚጠራው የሱዳን የሲቪል አስተዳድር ፖለቲከኞች ወታደራዊ አመራሩ ያወጣውን መግለጫ ማውገዛቸው ተሰምቷል።

የሱዳን ሉዓላዊ የሽግግር ምክር ቤት ፕሬዝዳንት እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል አብዱል ፈታህ አል ቡርሃን በሰጡት መግለጫ “የሰቪል አስተዳድር ፖለቲከኞች ለመፈንቅለ መንግስት ሙከራው ምክንያት ናቸው” ማለታቸው ይታወቃል።

ምክትል አዛዡ አህመት ዳጋሉ በበኩላቸው “ፖለቲከኞች የሱዳን ጦር አምባገነኑን የአልበሽር ስርዓት በመገርሰስ የከፈለውን መስዋዕት ረስተው ጦሩን ማናናቃቸው መፈንቅለ መንግስት እንዲፈጸም በር ከፍተዋል” ሲሉ የሲቪል አስተዳድሩን ተችተዋል።

የነፃነት እና የለውጥ ሀይል ጥምረት በመባል የሚጠራው የሲቪል አስተዳደር ባወጣው መግለጫ ሌተናል ጄኔራል አብዱል ፈታህ አል ቡርሃን እና ምክትል አዛዡ አህመት ዳጋሉ ንግግርን አውግዟል።

የሉዓላዊ የሽግግር ምክር ቤት ፕሬዝዳንት እና ምክትላቸው የከሸፈውን መፈንቅለ መንግስት አስመልክተው ያደረጉት ንግግር ወደ ዴሞክራሲ የሚደረገውን ሽግግር የሚጎዳ እና የሱዳንን አብዮት የሚቃረን ነው ብሏል።

“የሱዳን የሽግግር ጊዜ መሰረቶች እንዲናጉ አንፈቅድም” ያለው ጥምረቱ፤ ለዚህም ‹‹በሙሉ ሃይል›› እንደሚታገል ገልጧል፡፡

በሱዳን መከላከያ ሰራዊት እና የፀጥታ ሀይሉ ላይ የሚደረጉ የሪፎርም ስራዎች እንዲፋጠኑ የጠየቀው ጥምረቱ፤ “ርዝራዦች” ሲል የጠራቸው ሀይሎችን የማፅዳት ስራው ሊፋጠን ይገባልም ብሏል።

ጥምረቱ በመግለጫው አክሎም በመፈንቅለ መንግስት ሙከራው ላይ የሚደረገው የምርመራ ውጤት በአፋጣኝ ለህዝቡ ይፋ ሊደረግ ይገባል ያለ ሲሆን፤ በተግባሩ የተሳተፉ የሲቪል አመራሮች ዝርዝርም ይፋ እንዲደረግ ጠይቋል መባሉን የዘገበው አል ዐይን ነው።

በተያያዘ ዜና የቤጃ ጎሳ አባላት የሆኑ ተቃዋሚዎች ባነሱት ተቃውሞ የፖርት ሱዳን የአውሮፕላን ማረፊያን መዝጋታቸው ተሰምቷል።

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img