አምባ ዲጂታል፣ ሰኞ ነሐሴ 24፣ 2013 ― የደቡብ ሱዳን መንግሥት በሲቪል ማኅበራት ተጠርቷል የተባለውን የተቃውሞ ሰልፍ ተከትሎ ማኅበራዊ ሚዲያዎችን መዝጋቱን ሱዳን ትሪቡን ዘግቧል፡፡
ማኅበራቱ ጠርተውታል የተባለው ተቃውሞ በዛሬው እለት ይካሄዳል የተባለ ቢሆንም፣ መንግስት ቀኑ ከመድረሱ አስቀድሞ ከባለፈው ቅዳሜ አንስቶ ለቴሌኮም አገልግሎት ሰጪዎች ትእዛዝ በመስጠት ጥሪዎቹ የሚስተጋቡባቸው የማህበራዊ ትስስር መድረኮችን ዘግቷል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ጨምሮም ዜጎች ሕገ ወጥ ሲል የጠራውን የተቃውሞ ጥሪ እንዳይቀበሉ እያሳሰበ ቢገኝም፣ የተቃውሞው አዘጋጆች ግን ከእቅዳቸው ፍንክች እንደማይሉ ነው ያስታወቁት፡፡ የተቃውሞው ጥሪ መሪዎቹ ደጋፊ መተግበሪያዎችን ተጠቅመው መልእክት እያስተላለፉ ስለመሆናቸውም ተነግሯል፡፡
ተቃውሞውን የሚያስተባብሩ የማህበረሰብ አንቂዎች፣ ዜጎች አደባባይ ወጥተው መንግስት ላይ ተቃውሟቸውን እንዲያሰሙ ጥሪ ያቀረቡት፣ መንግስት ሙስናን እና የእርስ በርስ ግጭቶችን መግታት ተስኖታል፣ እንዲሁም የመናገር ነጻነትን እንዲያረጋግጥ ለመጠየቅ ነው፡፡