Sunday, October 6, 2024
spot_img

አዲስ ስታንዳርድ በመገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን የተጣለበትን እግድ በመቃወም ወደ ፍርድ ቤት ሊያመራ መሆኑ ተሰማ

አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ሐምሌ 10፣ 2013 ― ከሁለት ቀናት በፊት በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ፈቃዱ መታገዱን በመግለጽ ሥራ ማቆሙን ያሳወቀው አዲስ ስታንዳርድ ድረ ገጽ፣ የባለሥልጣኑን እግድ በመቃወም ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ሊወስደው ማቀዱን መስራችዋ ጸዳለ ለማ ነግረውኛል ብሎ ሬውተርስ ዘግቧል፡፡

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን በአዲስ ስታንዳርድ ላይ ስለወሰደው እርምጃ በሰጠው ማብራሪያ ድረ ገጹ፣ ‹‹በተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪ ተብሎ የተፈረጀውን ቡድን ‹የመከላከያ ኃይል› ብሎ እስከመጥራት›› መድረሱን አሳውቆ ነበር፡፡

ሆኖም ጸዳለ ለማ ባለሥልጣኑ የወሰደው እርምጃም ሆነ ‹‹ምክንያቱ ትክክለኛ ውሳኔ ነው ብለን ስለማናምን›› ወደ ፍርድ ቤት ለማምራት ማሰባቸውን መናገራቸው ነው የተመላከተው፡፡

የአዲስ ስታንዳርድ እግድ እስከ መጨረሻው የሚጸና መሆን ወይም አለመሆኑ ላይ ባለሥልጣኑ በሰጠው ማብራሪያው ባይገልጽም፣ ለአሻም ቲቪ የተናገሩት የባለሥልጣኑ ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክር አቶ አበራ ወንድወሰን ለምን ያህል ጊዜ እንደሆነ በትክክል ባናገሩም ‹‹ላልተወሰነ ጊዜ›› መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን የአዲስ ስታንዳርድን እግድ ተከትሎ የውጭ አገር ሚዲያዎች የትግራይን ጦርነት በሚዘግቡበት ወቅት ‹‹የትግራይ መከላከያ ኃይል›› ከማለት እንዲቆጠቡ ማሳሰቡም ተሰምቷል፡፡

የመገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ የሚሠሩ ዘገባዎችን ገምግሞም ሕወሓትን ብሔራዊ ሠራዊት እንዳለው በማድረግ የትግራይ መከላከያ ኃይል እያሉ የሚጠሩ አንዳንድ የውጭ ሚዲያዎች አሉ ያለ ሲሆን፣ የትግራይ ክልል ከኢትዮጵያ ፌዴሬሽን አንዷ አካል ናት ካለ በኋላ የመከላከያ ኃይል ሊኖራት አይችልም ሲል አብራርቷል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሕወሓትን ሽብርተኛ ብሎ ከመሰየሙ ጋር ተያይዞ እንዲህ አይነት ሥያሜዎችን መጠቀም የአገሪቱን የግዛት አንድነት፣ ብሔራዊ ጥቅምና ደኅንነት የሚጥስ መሆኑንም አመልክቷል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img