አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ሰኔ 17፣ 2013 ― ላለፉት 10 ወራት በእስር ላይ የቆዩት የወላይታ ዞን የቀድሞ አስተዳዳሪ አቶ ዳጋቶ ኩምቤ እና ምክትላቸው አቶ ጎበዜ ጎዳና በዛሬው እለት ከእስር መፈታታቸው ተነግሯል፡፡
ሁለቱ የቀድሞ አመራሮች ከእስር የተፈቱት በተከሰሱበት ወንጀል በፍርድ ቤት በነጻ ከተሰናበቱ በኋላ እንደሆነ ጠበቃቸው አቶ ተመስገን ዋጃና እንደነገሩት ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል፡፡
ሁለቱ አመራሮች የተከሰሱት ‹‹ሥልጣናቸውን አላግባብ የመገልገል›› ወንጀል ፈጽመዋል በሚል ነበር። በዚህ ክስ ስር የቀድሞው የወላይታ ዞን የፋይናንስ እና ኢኮኖሚ መምሪያ ኃላፊ አቶ ተከተል ጎአም ተካትተዋል። የሦስቱን ተከሳሾች ክስ ሲመለከት የቆየው የወላይታ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በዛሬው ውሎው፤ ተከሳሾቹ ወንጀሉን ባለመፈጸማቸው በነጻ እንዲሰናበቱ ብይን መስጠቱም በዘገባው ተመላክቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ የወላይታ ዞን የቀድሞ አስተዳዳሪ አቶ ዳጋቶ በተከሰሱበት ሁለተኛ መዝገብም ተመሳሳይ ውሳኔ መስጠቱን የተሰማ ሲሆን፣ በአቶ ዳጋቶ ላይ የቀረበው ሁለተኛ ክስ፤ ኢዩ ጩፋ ከተባለ ግለሰብ የጉቦ ገንዘብ በመቀበል የኢንቨስትመንት መሬት እንዲሰጣቸው አድርገዋል የሚል ነበር ተብሏል፡፡