አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ግንቦት 28፣ 2013 ― በእስር ላይ የሚገኙት የኦሮሞ ፌዴራሊስ ኮንግረስ አመራር አባሉ አቶ ጃዋር መሐመድ ፍርድ ቤት ጥርስ ሐኪም ጋር እንዲወሰዱ ከሁለት ወር በፊት ትእዛዝ ቢሰጥላቸውም እስካሁን ትእዛዙ አለመፈጸሙን ቤተሰቦቻቸው መናገራቸውን የኦሮሞ ታሳሪዎች ተከላካይ ጠበቆች አስታውቀዋል፡፡
ፖለቲከኛው ሕክምናውን ባለማግኘታቸውም ታምመው ምግብ ለመብላት መቸገራቸው ነው የተነገረው፡፡
ይህንኑ ተከትሎም የፓርቲ አጋራቸው የሆኑት እነ አቶ በቀለ ገርባ ‹አቶ ጃዋር ህክምና አግኝቶ መብላት እስኪችል እኛም አንበላም› በማለት የረሀብ አድማ መጀመራቸውን ጠበቆቹ ገልጸዋል፡፡
በዚሁ ሰበብ ቤተሰቦቻቸው የወሰዱላቸውን ምግብ ለመቀበል ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሊመለስ ችሏል ነው የተባለው፡፡