አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ግንቦት 17፣ 2013 ― የፊንፊኔ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ኩመላ ቡሳ የፊንፊኔ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት የኦሮሚያ ክልል መንግስት ፍርድ ቤቶች አደረጃጀት ሥልጣን እና ተግባር እንደገና ለመወሰን የወጣውን አዋጅ ቁጥር 216/2011ን መሠረት በማድረግ በይፋ ተከፍቶ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ነግረውኛል ብሎ ኦቢኤን ዘግቧል።
የአዲስ አበባ ከተማ የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤትና የክልሉ መንግስት መቀመጫ ከመሆኗ ጋር ተያይዞ የክልሉን መንግስት የተመለከቱ ወንጀል ነክና የፍትሃ ብሔር ጉዳዮች በዚህ ፍርድ ቤት ይታያል መባሉንም ዘገባው አመልክቷል።
በአዲስ አበባ ከተማ የሚኖሩ የኦሮሞ ብሔር ተወላጆችም ሕገ መንግስታዊ መብታቸውን በመጠቀም በዚህ ፍርድ ቤት በቋንቋቸዉ የመዳኘትና ተደራሽ የሆነ የፍትህ አገልግሎት የማግኘት መብትም ያገኛሉ ተብሏል።
በፍርድ ቤቱ የአገልግሎት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይም የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ የኦሮሚያ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ፣ የኦሮሚያ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ኮሚሽን ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችን ጨምሮ ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።