Sunday, September 22, 2024
spot_img

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኬንያ ቆይታቸው የኢጋድ አገራት መሪዎችን ያገኛሉ ተባለ

አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ኅዳር 7፣ 2014 ― በተያዘው ሳምንት በሦስት የአፍሪካ አሕጉር አገራት የሚያደርጉትን ጉብኝት የጀመሩት የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶንዮ ብሊንክን፣ ትላንት ማክሰኞ በደረሱባት ኬንያ ቆይታቸው የምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) አገራት መሪዎችን እንደሚያገኙ ተነግሯል፡፡

ብሊንክን ትላንት ማክሰኞ በጀመረው የአፍሪካ አህጉር ጉብኝታቸው፣ በተለይ በኬንያ ቆይታቸው የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ይመክራሉ መባሉን ዘ ኢስት አፍሪካን ዘግቧል፡፡

የአሜሪካውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በእንግድነት የተቀበሉት የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ፣ ባለፈው እሑድ ኅዳር 5፣ 2014 ለጥቂት ሰዓታት አዲስ አበባ ቆይተው መመለሳቸው ይታወቃል፡፡ ኬንያታ በአዲስ አበባ ቆይታቸው ፕሬዝዳንት ሳሕለወርቅ ዘውዴን እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን አግኝተዋል፡፡

አሁን አንቶንዮ ብሊንክንን የተቀበለችው ኬንያ ከቀናት በፊት የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልእክተኛው ጄፍሪ ፌልትማንን አስተናግዳለች፡፡ ፌልትማን በተመሳሳይ አዲስ አበባ ተገኝተው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ሌሎች ባለሥልጣናትን ማግኘታቸው ተነግሮ ነበር፡፡

በትግራይ ክልል ተጀምሮ አንድ ዓመት በተሻገረው የፌዴራል መንግስት እና የሕወሓት ጦርነት ተደጋጋሚ መግለጫዎችን የምታወጣው አሜሪካ፣ ተፋላሚ አካላት ጦርነቱን አቁመው ወደ ንግግር እንዲገቡ ስትጠይቅ ይስተዋላል፡፡ አገሪቱ ከቀናት በፊት በጦርነቱ ተሳትፎ ያላት ኤርትራ ላይ ማእቀብ የጣለች ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ላይ የምትጥለውን ማእቀብ ተፋላሚ አካላት ችግራቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ ከፈቱት በሚል እንዳዘገየችው አሳውቃለች፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img