Sunday, September 22, 2024
spot_img

በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ከ13 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የምግብ እጥረት ይገጥማቸዋል ሲል ተመድ አሳወቀ

አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ጳጉሜን 3፣ 2013 ― በመጪዎቹ ስድስት ወራት በኢትዮጵያ ተከስቶ ለረዥም ጊዜ በዘለቀው ጦርነት፣ በኮቪድ-19 ወረርሽኝ፣ በበረሃ አንበጣ፣ በገበያ አለመረጋጋት፣ በዋጋ ግሽበት፣ በድርቅና በጎርፍ አደጋ ምክንያት ከ13 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ለምግብ እጥረት አደጋ ሊጋለጡ እንደሚችሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የዓለም የምግብ ድርጅት አስታውቋል፡፡

የዓለም የምግብ ድርጅት በድረ ገጹ ባወጣው ሪፖርት፣ በኢትዮጵያ በመጪዎቹ ወራት ሊከሰት የሚችልን የረሃብ አደጋ ለማስታገስ 426 ሚሊዮን ዶላር ከለጋሽ ድርጅቶች እንደሚፈልግ አስታውቋል፡፡ አያይዞም በሰሜን የአገሪቱ ክፍል ሰባት ሚሊዮን ዜጎች ለረሃብ አደጋ መጋለጣቸውን ድርጀቱ ገልጿል፡፡

ድርጅቱ በተጨማሪም በዚሁ አካባቢ ከፌዴራል መንግሥቱና ከክልል ኃላፊዎች ጋር በመነጋገር በአፋር ክልል ለ530 ሺሕ ዜጎች፣ እንዲሁም በአማራ ክልል ለ250 ሺሕ ዜጎች በአፋጣኝ የዕለት ደራሽ ምግብ ለማቅረብ እየሠራሁ ነው ያለ ሲሆን፣ ነገር ግን ከለጋሾች የሚፈለገው የገንዘብ መጠን ካልተገኘ የድጋፍ ፈላጊዎች ቁጥርም ከፍ ሊል እንደሚችል አስታውቋል፡፡

የዓለም የምግብ ድርጅት ከለጋሽ አካላት የሚፈለገውን 426 ሚሊዮን ዶላር ካላገኘ፣ አሁን ዕርዳታ እየተደረገላቸው የሚገኙ አራት ሚሊዮን ዜጎች ሕይወት አደጋ ላይ ሊወድቅ እንደሚችል በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img