አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ ነሐሴ 21፣ 2013 ― የአፍሪካ ኅብረት ሊቀመንበር የሆኑት ሙሳ ማሕመት ፋቂ የቀድሞውን የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ኦሊሴጎን ኦባሳንጆን የኅብረቱ የምሥራቅ አፍሪካ ከፍተኛ ተወካይ አድርገው መሾማቸውን አስታውቀዋል፡፡
የኦባሳንጆ ሹመት የአፍሪካ ኅብረት በምሥራቅ አፍሪካ ቀጠና በሰላም፣ ፀጥታ፣ መረጋጋት እና የፖለቲካ ድርድር እንዲሰፍን የሚያደርገው እንቅስቃሴ አካል መሆኑን ሊቀመንበሩ በሹመቱ ደብዳቤ ላይ ገልጸዋል፡፡
የኅብረቱ አዲሱ ሹመኛ በተለይ በቀጣናው ዘላቂ ሰላም እና ፀጥታ እንዲሰፍን የሁሉም የፖለቲካ ተዋናዮች እና የባለድርሻ አካላት ተሳትፎን በማጠናከር ዙሪያ እንደሚሠሩ የገለጹት ሊመንበሩ፣ ሁሉም አካላት ለዚሁ ትብብር እንዲያደርጉም ጠይቀዋል፡፡
የቀድሞውን የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ኦሊሴጎን ኦባሳንጆ በቅርቡ በተካሄደው የኢትዮጵያ አገራዊ ምርጫ ወቅት የአፍሪካ ኅብረት ታዛቢ ቡድንን መርተው በታዛቢነት መገኘታቸው የሚታወቅ ነው፡፡