Sunday, September 22, 2024
spot_img

አሜሪካ ከሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ጋር በተገናኘ የኤርትራን ገዢ ፓርቲ እና ጦሩን ጨምሮ በሁለት ባለሥልጣናት ላይ ማዕቀብ ጣለች

አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ ኅዳር 3፣ 2014 ― የአሜሪካ ግምጃ ቤት የውጭ ሐብት ቁጥጥር ቢሮ ይፋ እንዳደረገው አገሪቱ ከሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ጋር በተገናኘ ገዢውን የፕሬዝዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ ፓርቲ ሕግዴፍ እና ጦሩን ጨምሮ በባለሥልጣናት ላይ ማዕቀብ መጣሏን አስታውቋል።

ግምጃ ቤቱ ባወጣው መግለጫ ላይ ማዕቀቡ ከኤርትራው ገዢ ፓርቲ ሕዝባዊ ግንባር ለዴሞክራሲ (ሕግዴፍ) እና ጦሩ በተጨማሪ የኤርትራ ብሔራዊ ደህንነት ቢሮ ሃላፊ አብርሃ ካሳ ነማርያም እና የፓርቲው የኢኮኖሚ ጉዳዮች አማካሪ ሐጎስ ገብረህይወት አካቷል።

ከነዚሁ ግለሰቦች ጋር ተያይዞም ሐጎስ በዋና ስራ አስፈፃሚነት የሚመሩት ሬድ ሲ ትሬዲንግ እና የፕሬዝዳንት ኢሳይያስ ፓርቲ የንግድ ተቋማትን በበላይነት የሚያስተዳድረው ህድሪ ትረስት የተሰኘ ድርጅት ማዕቀቡ ተጥሎባቸዋል።

ግምጃ ቤቱ ሁለቱ ድርጅቶች ላይ ማዕቀብ በመጣሉ፣ በአሜሪካ ውስጥ የሚገኝ ሐብታቸውን ከማንቀሳቀስ ታግደዋል።

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ከሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ጋር በተያያዘ ለሰላምና መረጋጋት እንቅፋት በሚሆኑ፣ የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦትን ወይም የተኩስ አቁም እንዳይደረግ በሚያደናቅፉ እንዲሁም ከባድ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን በሚፈጽሙ ግለሰቦችና አካላት ላይ ማዕቀብ ለመጣል የሚያስችል ትዕዛዝ በመስከረም ወር አጋማሽ መፈረማቸው አይዘነጋም።

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img