Monday, September 23, 2024
spot_img

በኢትዮጵያ የትኛውም ክልል እና የከተማ አስተዳደር የነዋሪነት መታወቂያ ላልተወሰነ ጊዜ እንዳይሰጥ ተከለከለ

አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ነሐሴ 13 2013 ― በኢትዮጵያ የትኛውም ክልል እና የከተማ አስተዳደር የነዋሪነት መታወቂያ ላልተወሰነ ጊዜ እንዳይሰጥ የከለከለው የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ መምሪያ ዕዝ ነው፡፡

በመላ አገሪቱ ከጥቅምት 23፣ 2014 ጀምሮ ለስድስት ወራት ተግባራዊ የሚሆን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተቋቁሞ፣ ዐዋጁን ለማስፈጸም በጠቅላይ ኢታማዦር ሹም የሚመራ የአስቸኳይ አዋጅ መምሪያ ዕዝ መቋቋሙ መነገሩ ይታወሳል፡፡

ይኸው ትላንት ጥቅምት 26፣ 2014 ሥራ የጀመረው የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ መምሪያ ዕዝ፣ የትኛውም ክልል እና የከተማ አስተዳደር የነዋሪነት መታወቂያ ላልተወሰነ ጊዜ እንዳይሰጥ የከለከለው በሁለት ክልሎች በአንድ የከተማ አስተዳደር መታወቂያ በሕገ ወጥ መንገድ እየተሰጠ መሆኑን ደርሼበታለሁ በሚል ነው፡፡

እዙ በሕገ ወጥ መንገድ የነዋሪነት መታወቂያ እየተሰጠ ነው ያለው በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች፣ እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ነው፡፡ በሌላ በኩል የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ መምሪያ ዕዝ ‹‹በተደረገላቸው የክተት ጥሪ መሠረት›› በአሁኑ ወቅት በግንባር ከተሰለፈና ለመዝመት ከተመዘገበ ሰው ውጭ በክልል ከተሞች፣ በዞንና ወረዳ ከተሞች፣ በከተማ አስተዳደሮች፣ እንዲሁም በከተማ ደረጃ በሚታዩ ሌሎች ከተሞች የሚገኝ ማንኛውም መሣሪያ የያዘ ሰው በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ መሣሪያውን እንዲያስመዘግብ መታዘዙን አስታውሶ፣ በተጠቀሱት መስተዳድሮች የሚገኙ ኃላፊዎችም በቀልጣፋ አገልግሎት ይሄንኑ እንዲያስፈጽሙ ግዴታ እንደተጣለባቸው ገልጧል፡፡

በዚሁ መግለጫው፣ ‹‹የገባንበትን የህልውና ጦርነት መመከት የሚቻለው ኢኮኖሚያችንን በማሳደግና ዜጋው የሚጠበቅበትን ግዴታ ሲወጣ ነው›› ያለው እዙ፣ ጊዜው የግብር መክፈያ ወቅት ስለሆነ፣ ኢትዮጵያውያን ለሀገራቸው ሕይወታቸውን ለመስጠት በወሰኑበት በዚህ ጊዜ፣ ግብር ከፋዩ ማኅበረሰብ ለሚወዳት ሀገሩ ተገቢውን ግብር በተገቢው ጊዜ በመክፈል ግዴታውን እንዲወጣ ያሳሰበ ሲሆን፣ ‹‹ግብር ከፋዩ ማኅበረሰብ ግብር እንዳይከፍል በሚቀሰቅሱትና በሚያሸብሩት ላይ ሕጋዊ ርምጃ እንዲወሰድባቸው›› መታዘዙንም ነው ያመለከተው፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተያዘው ሳምንት ማክሰኞ ጥቅምት 23፣ 2014 የታወጀመው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አስመልክቶ ባሰፈሩት ማስታወሻ ‹‹አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የታወጀው የመከራውን ጊዜ ለማሳጠርና የመፍትሔውን ጊዜ ለማቅረብ ነው›› ብለው ነበር፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img