መሐመድ አወል ሳላሕ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ
ቀድሞ በሙዚቃ ሥራዎቹ ኋላም በእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ ለአድማጮች ባደረሳቸው መንፈሣዊ የነሺዳ ሥራዎች የሚታወቀው መሐመድ አወል ሳላሕ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡
በ1958 በወሎ ክፍለ ሐገር ደሴ ከተማ የተወለደው መሐመድ አወል ሳላሕ፣ እስከ ስምንተኛ ክፍል የዘለቀውን ትምህርቱን በዚያው ተከታትሏል፡፡ በማስከተልም ወደ አስመራ በማቅናት በጦር ሠራዊት ውስጥ መቀላቀሉን የሕይወት ታሪኩ ያመለክታል፡፡
ከአስመራ ወደ አዲስ አበባ የተመለሰው መሐመድ አወል ሳላሕ፣ ለጥቂት ጊዜያት ወደ ሳዑዲ አረቢያ ያቀና ቢሆንም ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ ‹‹ከመከም›› የተሰኘውን አልበም ወደ አድማጮች አድርሷል፡፡
በ1990ዎቹ አጋማሽ የሙዚቃ ሥራዎችን በመተው ወደ መንፈሣዊ ሥራዎች የተመለሰው መሐመድ አወል ሳላሕ፣ በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ በብዛት የተደመጡና የተወደዱ የነሺዳ አልበሞችን ማድረሱም ይነገርለታል፡፡
መሐመድ አወል ሳላሕ ባለትዳር እና የስድስት ልጆች አባት ነበር፡፡