አምባ ዲጂታል፣ እሑድ ነሐሴ 9፣ 2013 ― የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለአዲስ ባንኮች ያስቀመጠው ቀድሞ በነበረው በ500 ሚሊዮን ብር ካፒታል ባንክ የመመስረቻ ጊዜ ላይ ተጨማሪ ጊዜ እንደማይፈቅድ አስታውቋል፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት የአዲስ ባንኮች መመስረቻ ካፒታል ወደ 5 ቢሊዮን ብር እንዲያድግ መመሪያ ያወጣው ብሔራዊ ባንክ ከመመሪያው ቀድመው አክሲዮን በመሸጥ ላይ የነበሩ ባንኮች እስከ መስከረም የመጀመሪያ ቀናት ድረስ ቀድሞ በስራ ላይ የነበረውን የ500 ሚሊዮን ብር መመስረቻ ካፒታሉን እንዲያጠናቅቁ የጊዜ ገደብ አስቀምጦ ነበር፡፡
ሆኖም በምስረታ ላይ ያሉ ሰባት ባንኮች የጊዜ ገደቡ ይጨመርልን በሚል ለብሔራዊ ባንክ ደብዳቤ ቢጽፉም፣ ባንኩ ግን ይህን ማድረግ እንደማይችል አሳውቋቸዋል መባሉን የፎርቹን ዘገባ ያመለክታል፡፡
ይህንኑ ተከትሎ በምስረታ ላይ ከሚገኙት ባንኮች መካከል ጃኖ፣ አፍሮ እና ግዕዝ የተሰኙ ባንኮች የተቀመጠውን መመስረቻ በጊዜው ለማሟላት ሲሉ ተጣማሪ እንደሚፈልጉ ወይም ለመፍረስ እንደሚገደዱ ነው የተነገረው፡፡
በምስረታ ላይ ከሚገኙት ባንኮች መካከል በወለድ አልባ አገልግሎት ላይ የሚሰማሩት ዛድ እና ራሚስ የተሰኙት ሁለት ባንኮች ቀድሞው መጣመራቸው መነገሩ የሚታወስ ነው፡፡