አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ነሐሴ 4፣ 2013 ― በሳዑዲ ዐረቢያ በኢትዮጵያውያን ላይ የሚደርሰው እስር እና ወከባ እንዲቆም በአገሪቱ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሌንጮ ባቲ ጠይቀዋል፡፡
አምባሳደር ሌንጮ ባቲ ይህን ያሉት ከሳኡዲ ዐረቢያ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ዴኤታ ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት መሆኑን በሪያድ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አስታውቋል፡፡
አምባሳደር ሌንጮ ባቲ በሳኡዲ አረቢያ በኢትዮጵያዊያን ላይ የሚደረገው አፈሳ እንዲቆም በጠየቁበት ወቅት፣ የሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ዴኤታ አሕመድ ቀጣን በበኩላቸው ከሳኡዲ አረቢያ አገር ግዛት ሚኒስቴር ጋር ተነጋግረው ይኸው እስራት እንዲቆም አዎንታዊ ምላሽ እንደሚሰጡ ቃል ገብተዋል ነው የተባለው።
ባለፉተ ወራት በሳዑዲ ዐረቢያ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ እስር እና ወከባ ሲደርስ እንደነበር መነገሩ ይታወሳል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒቴር በበኩሉ በርካታ ሺሕ ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው ሲመልስ መሰንበቱን ማሳወቁም አይዘነጋም፡፡