Sunday, September 22, 2024
spot_img

መንግስት የወሰነውን የተናጠል ተኩስ አቁም እያከበረ ለትንኮሳዎች ምላሽ ይሰጣል ሲሉ ጠ/ሚ ዐቢይ ገለጹ

አምባ ዲጂታል፣ ሰኞ ሐምሌ 12፣ 2013 ― የፌዴራል መንግስት የወሰነውን የተናጠል ተኩስ አቁም እያከበረ ለሚሰነዘሩበት ትንኮሳዎች ግን ተገቢውን ምላሽ እንደሚሰጥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አስታወቀዋል።

የሀገር መከላከያ ሰራዊትና የክልል የጸጥታ ኃይሎች አሁን ላይ ተገቢውን ቦታ እየያዙ እየያዙ መሆኑን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህን ለማወክ ትንኮሳ ሊሰነዘር እንደሚችል ገልጸዋል።

መንግስት የገባውን የተኩስ አቁም እያከበረ ለሚሰነዘር ትንኮሳ ግን ተገቢውን ምላሽ እንደሚሰጥ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ላይ አስፍረዋል።

“የገጠምነው ጠላት የኢትዮጵያ ነቀርሳ የሆነውን ጠላት ነው፤ ጁንታው ያገኘውን የፖለቲካ ሥልጣን የገዛ ሀገሩን ለማፍረስ የተጠቀመ ምናልባት በታሪክ ብቸኛው ቡድን ነው” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፤ “አብሮ የኖረ ሰይጣን በቶሎ አይነቀልም እንደሚባለው በግራ በቀኝ መፍጨርጨሩ አይቀርም” ብለዋል።

“የህወሃት ሃይል በርግጠኝነት መልሶ እንዳይበቅል ሆኖ ይነቀላል“ ሲሉ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ የሚሆነው ሁላችንም እንቦጩን ለመንቀል ከተረባረብን ነው“ ብለዋል።

ግለሰቦች ሊሳሳቱ እንደሚችሉ እና ሐሳብ የሚከፋፍሉ መረጃዎችም ሊሰሙ እንደሚችሉም የገለጹ ሲሆን በአካሄድ ላይ ክርክሮች ቢፈጠሩም በግብ አንድ መሆን እንደሚያስፈልግ አንስተዋል።

ኢትዮጵያውያንን ከግብ የሚያነጣጥል እንደሌለ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፤ “ የህወሃትን ዕቅድ ለመቀልበስ“ የኢትዮጵያ ልጆች ከሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች መነሳታቸውንና ይህም በራሱ ድል እንደሆነም አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያውያን አሁን ላይ የሀገራቸው ጠላት ማን እንደሆነ ማወቃቸውንና ለዚህም ምን ማድረግ እንዳለባቸው መረዳታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

በዚህም መሰረት ኢትዮጵያውያን ለዚህ ምን መደረግ እንዳለባቸው ማወቃቸውንና እንደሚየደርጉትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አረጋግጠዋል።

የሀገር መከላከያ ሰራዊትና የክልል ልዩ ኃይሎች አሁን ላይ ተገቢውን ቦታ እየያዙ መሆኑን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ምንን፣ ለምን፣ እንዴት፣ የትና መቼ መደረግ እንዳለባቸው ጥብቅ ዕቅድ መኖሩንም አስታውቀዋል።

በዚህም ውጤቱን በጥቂት ጊዜ ውስጥ “ወዳጅም ጠላትም ያየዋል” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሰራዊቱ አስፈላጊ ሲሆን “እጅን በአፍ ላይ ለሚያስጭን“ ላሉት ተልዕኮ መዘጋጀቱን አስታውቀዋል።

“አረሙ እንዲነቀል አድርገን እንሠራለን። አረሙን ስንነቅል ግን ስንዴውን እንዳንጎዳው የሚቻለውን ሁሉ ጥንቃቄ እናደርጋለን“ ሲሉ የገለጹ ሲሆን “በኢትዮጵያ ባህል አረም በደቦ ነው የሚነቀለው“ ብለዋል።

አሁን ላይ ኢትዮጵየውያን በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ የኢትዮጵያ ያስፈራቸዋል ያሏቸው ኃይሎች የሚከፋፍል የመሰላቸውን ነገር ሁሉ እያደረጉ ስለመሆኑ ጠቅሰዋል።

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img