አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ሐምሌ 7፣ 2013 ― የአዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በትግራይ ተወላጆች ላይ እስር እየተፈጸመ መሆኑን ያመለከተው አረና፣ እየተፈጸመ ነው ያለው እስር እና የንግድ ድርጅቶች መዘጋት እንዲቆም ጠይቋል፡፡
የፓርቲው የማእከላዊ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ ሐፍታይ ገብረሩፋኤል ለዶይቸ ቬለ እንደተናገሩት በሺሕዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ ሲታሰሩ፣ ሱቆችም በመዘጋታቸው በርካታ የትግራይ ተወላጆች ከሥራ ውጭ ሆነዋል፡፡
ከእስሩ ጋር በተገናኘ ያስረዱት አቶ ሐፍታይ፣ ፖሊሶች የኤርትራ እና የትግራይ ተወላጆች መለየት ስለማይችሉም ኤርትራዊያኑን ካሰሯቸው በኋላ እንደሚለቁ ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ፓርቲው ባወጣው መግለጫ፣ በአሁኑ ወቅት በትግራይ የተፈጠረው ችግር በንግግር ብቻ እንደሚፈታ በመግለጽ፣ መንግስት ያወጀው የተኩስ አቁም በሁለቱም ተፋላሚ ኃያሎች በሰነድ ተቀምጦ መተግበር አለበት ብሏል።