Sunday, September 22, 2024
spot_img

የአውሮፓ ኅብረት ኃላፊ በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ እንዲጣል መጠየቁ ተሰማ

አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ሐምሌ 6፣ 2013 ― የአውሮፓ ኅብረት የውጭ እና የደኅንነት ጉዳይ ኃላፊ ጆሴፍ ቦሬል አባል አገራት በትግራይ ክልል ባለው ቀውስ ምክንያት በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ ለመጣል እንዲያስቡ መጠየቃቸው ተሰምቷል፡፡

ኃላፊው ‹‹በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ በእጃችን ያሉ አማራጮችን ከግምት ውስጥ ማስገባት ይጠይቃል የሚል እምነት አለኝ፤ እናም እኔ እስከገባኝ ድረስ የመገደብ እርምጃዎች አማራጭ ጠረጴዛው ላይ መቀመጥ አለበት›› በማለት በብራስልስ በተካሄደው የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳዮች ሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ መናገራቸውን የቢቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ቦሬል የአውሮፓ ኅብረት የኢትዮጵያ መንግሥት ያወጀው የተኩስ አቁም ስምምነት መሬት ላይ እንዲተገብር እንደሚፈልግ የገለጹ ሲሆን፣ ክልሉ በአንፃሩ ከሌላው ዓለም ጋር እየተቆራረጠ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

የአውሮፓ ኅብረት ኃላፊው ከሳምንት በፊት ‹‹የተኩስ አቁም ማለት የክልሉን መብራት መቁረጥ እና አስፈላጊ የሚባሉ መሰረተ ልማትን ማውደም አይደለም›› በማለት ተችተው ነበር፡፡

በተመሳሳይ መንግሥት ያወጀው ‹‹ተኩስ አቁም ሳይሆን ከበባ ነው፤ ረሃብም እንደ ጦር መሳሪያ እያገለገለ ነው›› በማለት የአውሮፓ ኅብረት የቀውስ ጉዳዮች ኮሚሽነር ጃኔዝ ሌናርቺክ ለኅብረቱ ፓርላማ በሰጡት ገለፃ ተችተዋል።

በብራስልስ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ የኮሚሽነሩን ንግግግር አሳዛኝ በማለት፣ ‹‹ከበባ ነው›› መባሉንም ውድቅ እንዳደረገው ለቀረበው ክስ በሰጠው ምላሽ ላይ አስፍሯል።

አሁሁ ኃላፊው ማእቀብ የጠየቁት የአውሮፓ ኅብረት፣ ለኢትዮጵያ የሚያደርገውን ቀጥተኛ የበጀት እርዳታን ያገደ ሲሆን፣ የእርዳታ ሠራተኞችንም የሚያደናቅፉ ባለስልጣናትንም ጥቁር መዝገብ ውስጥ አካትታለሁ በሚል ማስጠንቀቁን የኅብረቱ ልሳን ‹ኢዩ ኦብዘርቨር› ባወጣው ዘገባ ማመልከቱንም የቢቢሲ ዘገባ ያሳያል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img