አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ሐምሌ 1፣ 2013 ― የኢትዮጵያ መንግሥት በተለያዩ አገራት የሚገኙ በርካታ ዲፕሎማቶችን ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ መጥራቱን አዲስ ስታንዳርድ ይዞት የወጣው መረጃ ያመለክታል፡፡
የዜና ወኪሉ ይዞት በወጣው ዘገባ በዋሺንግተን በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ውስጥ የሚሠሩ 18 ባልደረቦች እንዲሁም፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ አምስት ባልደረቦች ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ተደርገው የሠራተኞቹ ቁጥር ወደ ሦስት ዝቅ ተደርጓል፡፡
በተጨማሪም የሎስ አንጀለስ፣ ፈራንክፈርት እና ሚኒሶታ ቆንስላዎች ስለሚዘጉ ሠራተኞቹም ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ጥሪ ተደርጎላቸዋል፡፡
እነዚህ ውሳኔዎች የተሰሙት በሳምንቱ መጀመሪያ ሰኞ በፓርላማ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት ሁኔታ በርካታ ቁጥር ያላቸው ኤምባሲዎች እንዲኖራት አይፈቅድም ማለታቸውን ተከትሎ ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ አሁን ካሉት ኤምባሲዎች ቢያንስ 30 ያህሉ መቀነስ ይገባቸዋል ያሉ ሲሆን፣ አምባሳደሮቹ በአገራቸው ተቀምጠው ስራቸውን እንዲሰሩ ማድረግ ይገባል ሲሉ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥቆማ ሰጥተው ነበር፡፡