አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ሰኔ 29፣ 2013 ― ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ምርጫ ቦርድ በአዲስ አበባ ከተማ የተደረገውን የምርጫ ውጤት ‹‹አሳማኝ ባልሆነ ምክንያት ይፋ ከማድረግ ዘግይቷል›› ሲል ባወጣው መግለጫ ወቅሷል፡፡
ፓርቲው በመግለጫው ‹‹የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤትን ይፋ ከማድረጉ በፊት ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ውጤቱን ከመግለጽ እንዲቆጠቡ የሚከለክል ሕጋዊ ድንጋጌ በመኖሩ፣ እስካሁን ለሕግ ተገዥ በመሆን በድምጽ መስጫ ቀን የነበሩትን ችግሮች እና ውጤቱን በሚመለከት መግለጫ ከመስጠት ተቆጥቦ›› መቆየቱን አመልክቷል፡፡
‹ሆኖም ቦርዱ እስካሁን በተወሰኑ የአገሪቱ ክልሎች ያሉ ውጤቶችን ይፋ ከማድረጉ በስተቀር፣ ‹‹በተሻለ መረጋጋት ውስጥ ተደርጓል ያለውን የአዲስ አበባ ከተማን ውጤት ‹‹አሳማኝ ባልሆነ ምክንያት ለህዝብ ይፋ ሳያደርግ ጊዜ እየወሰደ እንደሆነ›› ፓርቲው እንደሚያምንም ገልጧል፡፡
አክሎም ‹‹ቦርዱ ውጤቱን ያፋ ሳያደርግ በተድበሰበሰ ሁኔታ መቆየቱ አላስፈላጊ ለሆኑ እንቅስቃሴዎች በር የሚከፍት›› ነው ያለ ሲሆን፣ ‹‹አዲስ አበባን በተመለከተ በቦርዱ እጅ የገባው ውጤት የአንድ ፓርቲን የበላይነት እንደከዚህ በፊቱ የሚያረጋግጥ ሆነም አልሆነም፣ ፓርቲውና እና ህዝቡ እውነቱን የማወቅ መብት ስላላቸው››፣ የቦርዱን ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳን ‹‹የአዲስ አበባን ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ለመራጩ ህዝብ ይፋ ያድርጉ›› ሲል ጥሪ አቅርቧል፡፡
ፓርቲው በመግለጫው ማሳረጊያ፣ ‹‹ቦርዱ ውጤቱን ይፋ ለማድረግ ምክንያታዊ ያልሆነ ጊዜ አሁንም መውሰዱን የሚቀጥል ከሆነ፣ በእጄ አለ ያለውን ‹‹የጥናት ሪፖርት›› ለሕዝብ ይፋ ለማድረግ እና ‹‹ለቀጣይ ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ለመግባት›› እገደዳለሁ ሲል አሳውቋል፡፡