አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ ሰኔ 25፣ 2013 ― የፌዴራል ፖሊስ የአውሎ እና የኢትዮ ፎረም ጋዜጠኞች የታሠሩት በሙያቸው ሳይሆን በሽብርተኝነት ከተፈረጀው ሕወሃት ጋር ባላቸው ግንኙነት ነው ማለቱ ተሰማ። ይህንኑ የኮሚሽኑ የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊ ጄይላን ዐብዲ ነግረውኛል ብሎ አዲስ ስታንዳርድ አስነብቧል።
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለሥልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ ዮናታን ተስፋዬ በበኩላቸው የጋዜጠኞቹን እስር በሚመለከት ባለሥልጣኑ እንደማያውቅ መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል።
የጋዜጠኞቹ ጠበቃ የሆኑት ታደለ ገብሬ ከሁለቱ ሚዲያዎች በአጠቃላይ 12 ባለሞያዎች መታሠራቸውን ያመለከቱ ሲሆን፣ ነገር ግን እስካሁን ድረስ ደንበኞቻቸውን ማግኘት እንዳልቻሉ ገልፀዋል።
አክለውም ጋዜጠኞቹ በዛሬው እለት ወደ አራዳ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተወስደዋል ተብለው ከሥፍራው ቢያቀኑም እንዳልነበሩም አሳውቀዋል።
ባለፉት ሁለት ቀናት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል የሆኑት በቃሉ አላምረው እና ያየሰው ሽመልስ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ታስረው በዋስ የተፈቱ መሆናቸውን ዘገባው አስታውሷል።
የፎቶ ምንጭ፡ አዲስ ስታንዳርድ