አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ሰኔ 19፣ 2013 ― የአሜሪካው የረድኤት ድርጅት አስተዳዳሪዋ ሳማናታ ፓወር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በሳምንቱ መጀመሪያ በትግራይ ረሐብ የለም ማለታቸውን ‹‹ሐሰት ነው›› ብለውታል፡፡
ሳማንታ ፓወር የሚመሩት ዩኤስኤድ በትግራይ ጉዳይ አዲስ ግኝት እንዳለው ያመለከቱ ሲሆን፣ በግኝቱ መሠረት እስከ 900 ሺሕ ሰዎች ረሐብ ተጋርጦባቸዋል ብለዋል፡፡
የዩኤስኤድ ኃላፊ ከዚህ ቀደም የአሜሪካ እና የአውሮፓ ኅብረት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ባደረጉት ስብሰባ የኖቤል ተሸላሚው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ በትግራይ ክልል ‹‹ጥቃት ካላስቆሙ እና የኤርትራን ሠራዊትን ካላስወጡ፤ በኢትዮጵያ የረሐብ ታሪክን በመድገም የሚታወሱ መሪ ይሆናሉ›› ማለታቸው ይታወሳል፡፡
የትግራይ ክልልን አስመልክቶ ከሳምንት በፊት ሥልጣን የለቀቁት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ ጉዳዮችና የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ባለሥልጣን ማርክ ሎውኮክ፣ በተመሳሳይ በክልሉ ረሐብ እንደተከሰተ መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ሆኖም የብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽነር አቶ ምትኩ ካሳ፤ እንዲህ የመባሉን ሪፖርት አስተባብለዋል፡፡