Sunday, September 22, 2024
spot_img

ኢትዮጵያ ግብፅ እና ሱዳን ለጸጥታው ምክር ቤት ያቀረቡትን የስብሰባ ጥሪ ተቃወመች

አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ ሰኔ 18፣ 2013 ― ኢትዮጵያ ባሳለፍነው ረቡዕ ግብፅ እና ሱዳን ለጸጥታው ምክር ቤት ላቀረቡት የስብሰባ ጥሪ ምላሽ ሰጥታለች፡፡

በምላሿ ጥሪው ለአፍሪካ ኅብረት ጥረት ዋጋ ያልሰጠና ያላከበረ ነው ያለችው ኢትዮጵያ፣ ጥሪውን እንደማትቀበል አስታውቃለች፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ ጥሪው ‹‹የተጀመረውን አፍሪካ ህብረት መር ድርድር ወደ ጎን በመተው›› የቀረበ ነው ሲል ለምክር ቤቱ ፕሬዝዳንት ግልፅ ደብዳቤ ጽፏል፡፡

በደብዳቤው የሀገራቱ አቋም ልክ እንደካሁን ቀደሙ ሁሉ የተቀናጀና የአፍሪካ ኅብረትን ጥረት ለማጣጣል የሚደረግ ብሎም፣ በሶስቱም ሀገራት መካከል ያለውን መተማመንን ይበልጥ የሚሸረሽር እንደሆነ ገልጿል፡፡ ሚኒስቴሩ ደብዳቤውን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ በአፍሪካ ህብረት መሪነት ድርድር ከተጀመረበት ወቅት አንስቶ ሀገራቱ ተደጋገሚ ሂደቱን የማደናቀፍ ተግባራት ሲያከናውኑ ቆይተዋልም ነው ያለው፡፡

መግለጫው “ግብፅና ሱዳን እስካሁን አላስፈላጊ አጀንዳዎች በማንሳት ውይይቶችን ማወሳሰብ፣ አጀንዳውን ከደህንነት ጋር ማገናኘነት እና ዓለም አቀፋዊ ማድረግ፣ ዓረብ ሊግ በጉዳዩ ላይ ጣልቃ እንዲገባ ሲጎትቱና በርካታ አደናቃፊ ዘዴዎችን ሲጠቀሙ ነበሩ”ም ብሏል፡፡

ይህ አካሄድ የወቅቱን የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፕሬዝዳንት ፌሊክስ ሼስኬዲን ቀና እና ተስፋ ሰጪ ጥረትን ያባከነ እና ሂደቱን የማራዘም ተግባራቸው እንደቀጠሉበት የሚያመላክት ነው ሲልም አክሏል በመግለጫው፡፡

“ትብብርን ያጠናክራሉ ተብለው የተጀመሩ የሶስትዮሽ ድርድሮች ግብፅና ሱዳን የቅኝ-ገዥ ውሎች ብቸኛ መብቶቻቸው እና በኢትዮጵያ ያላቸውን ምኞት ማሳኪያ መንገዶች መሆን የለባቸውም”ም ብሏል ሚኒስቴሩ፡፡

ሀገራቱ በተናጠል የሚደረግ የውሃ ሙሌት እንዲቆም የጸጥታው ም/ቤት ኢትዮጵያን እንዲያሳስብ በማለት ላቀረቡት ጥረትም የኢትዮጵያ መንግስት ቀደም ብሎ በተደረሰው የሶስትዮሽ ስምምነት መሰረት ሁለተኛውን ሙሌት ለማከናወን የያዘው መርሀ-ግብር እንደተጠበቀ መሆኑና የሚለወጥ ምንም አዲስ ነገር እንደሌለ ግልፅ አድርጓል፡፡

የኢትዮጵያን አቋም ግልፅ ያደረገው መግለጫው፤ የጸጥታው ም/ቤት ግብፅና ሱዳን የሚከተሉትን አካሄድ ትተው በአፍሪካ ህብረት ጥላ ስር ወደ ተጀመረው ድርድር በቀና መንፈስ እንዲመለሱ ያበረታታቸው ሲልም ጥሪ አቅርቧል፡፡

ሱዳን እና ግብፅ ከትናንት በስቲያ ረቡዕ ምክር ቤቱ በግድቡ ጉዳይ እንዲሰበሰብ ጥሪ ማቅረባቸው ይታወሳል፡፡

ጥሪው በሱዳኗ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማሪያም ሳዲቅ አል-ማህዲ በተጻፈ ደብዳቤ የቀረበ ነው፡፡

ማሪያም ሳዲቅ ግድቡ “በሚሊዮኖች በሚቆጠሩ ሰዎች ደህንነት ላይ ተጽዕኖ ያሳድራል” ሲል በሚያትተው ደብዳቤያቸው ተጽዕኖውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ኢትዮጵያ በተናጠል ልታደርግ የተዘጋጀችው የሁለተኛ ዙር ሙሌት እንዲቆምና ምክር ቤቱ
ከግምት በማስገባት እንዲሁም በተናጠል የሚደረግ የውሃ ሙሌት እንዲቆም የጸጥታው ም/ቤት ኢትዮጵያን እንዲያሳስብ የሚጠይቅ ይዘት ያለው ደብዳቤም መጻፉ የሚታወስ ነው፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img