አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ሰኔ 2፣ 2013 ― በተባበሩት መንግሥታት እና በተራድኦ ወኪሎች ተንታኞች ተሠርቷል በተባለ ግመታ በትግራይ ክልል 350 ሺሕ ሰዎች በረሃብ ቀጠና ውስጥ እንደሚገኙ ሬውተርስ ተመልክቼዋለሁ ያለውን ሰነድ ዋቢ አድርጎ ዘግቧል፡፡
የዜና ተቋሙ ተመልክቼዋለሁ ባለውና የተራድኦ ወኪል የመረጃ ተንታኞች ተጠቅመውበታል በተባለው ኢንተግሬትት ፉድ ኢንሴኩሪቲ ፌዝ ክላሲፊኬሽን ወይም አይ አይፒሲ መሠረት አንድ አካባቢ የረሐብ ቀጠና ውስጥ ነው የሚባለው በአካባቢው ካሉ ሰዎች 20 በመቶ የሚሆኑት ሰዎች ሙሉ በሙሉ ለምግብ እጥረት ሲጋለጡና የሞት ምጣኔውም ከአስር ሺሕ ሰዎች መካካል ሁለት ሲሆን ነው፡፡
ሆኖም ይኸው በዛሬው እለት በዲፕሎማቶች በኩል ይፋ ይደረጋል የተባለውን ሰነድ በተመለከተ ሬውተርስ አናገርኳቸው ያላቸው መቀመጫቸውን ኒውዮርክ ያደረጉ የኢትዮጵያ ዲፕሎማት ግን የተባለውን ጥናት የመረጃ አሰባሰቡን እንደሚጠራጠሩት ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት እና ሥራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነሩ አቶ ምትኩ ካሳ በትላንትናው እለት በሰጡት መግለጫም በትግራይ ክልል ረሃብ ሊከሰት ይችላል መባሉን ትክክል አይደለም ብለው ነበር፡፡
ኮሚሽነሩ በክልሉ የሰብአዊ አቅርቦት 90 በመቶ ለሚሆኑ ሰዎች መዳረሱን በመጥቀስም፣ በአንዳንድ ቦታዎች የሕወሃት ርዝራዥ ያሏቸው አቅርቦቱን እንደሚያደናቅፉ ተናግረዋል፡፡
በትግራይ ክልል ረሀብ ሊከሰት ይችላል የሚለው ስጋት ከሰሞኑ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ በሆኑት አንቶንዮ ጉቴሬዝ ጨምሮ በተለያዩ የውጪ አካላት ሲስተጋባ መሰንበቱ የሚታወቅ ነው፡፡