አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ሰኔ 1፣ 2013 ― የአለም ጤና ድርጅት በአፍሪካ ላይ ባንዣበበው 3ኛው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ዙሪያ አፍሪካም አልተዘጋጀችም ብሏል፡፡
ድርጅቱ የአፍሪካ ዳይሬክተር ዶክተር ማትሺዲሶ ሞይቲ በሰጡት መግለጫ 3ኛው የኮሮና ወረርሽኝ ሊከሰት ይችላል ሲሉ ማስጠንቃቸውን ሲጂቲኤን ዘግቧል፡፡
3ኛው የኮሮና ወረርሽን ስጋት መጋረጡን የጠቆሙት ዳይሬክተሯ፣ ቫይረሱን ለመከላከል ያለው የመጨረሻ ሕክምና መከላከል ነው ብለዋል፡፡
ዳይሬክተሯ የአፍሪካ ሀገራት የጥንቃቄ አቅማቸውን በማጠናከር የሆስፒታሎችን መጨናነቅ ማስቀረት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ እንደ ዳይሬክተር ሞይቲ ከሆነ ለአፍሪካ ሀገራት የሚደረገው የክትባት አቅርቦትም ሊቆም መቃረቡን ነው የገለጹት፡፡
‹‹ከአፍሪካ ውጭ ያሉ ብዙ ሀገራት አሁን ከፍተኛ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የህብረተሰብ ክፍሎችን›› እየከተቡ ሲሆን፣ ልጆችንም ለመከተብ እያሰቡበት ይገኛሉ ያሉት ሞይቲ፣ በአንጻሩ አፍሪካ ግን ዝግጁ አለመሆኗንና በክትባት አቅርቦት ላይ ያሉ ማነቆዎች እንዳስጨነቃቸው ተናግረዋል፡፡
ሞይቲ 24 ከመቶ የሚሆነው የዓለም ሕዝብ በአሁኑ ጊዜ ክትባት የወሰደ ሲሆን፣ በአፍሪካ ግን እስካሁን ድረስ 2 በመቶ የሚሆን ህዝብ ብቻ አንድ ጊዜ መከተቡን ተናግረዋል፡፡
በአፍሪካ የቫይረሱ ስርጭት ከባለፉት ሁለት ሳምንታት ጋር ሲነፃፀር የ20 በመቶ ጭማሪ መመዝገቡንም አመለክተዋል፡፡