አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ሰኔ 1፣ 2013 ― ኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ላለፉት 20 ዓመታት ህወሓትን የደገፉት የአሜሪካ አስተዳደሮች በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ለተፈጠረው ጦርነት ተጠያቂ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
ሚኒስትሩ ኡስማን ሳሌህ ለተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት በጻፉት ደብዳቤ፣ ኤርትራን በጦርነቱ መወንጀል መሠረተ ቢስ ነው ሲሉም ገልጸዋል፡፡
ዑስማን ሳሌህ በደብዳቤያቸው ላይ የፕሬዝዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር፣ በክልሉ ጣልቃ በመግባት እና በማስፈራራት ‹‹ተጨማሪ ግጭቶችን እና አለመረጋጋትን እያስከተለ ነው›› ሲሉ ከሰዋል፡፡ ‹‹የእነዚህ ድርጊቶች ግልፅ ዓላማ የህወሓትን አገዛዝ ቅሪቶች እንደገና ለማደስ ነው›› ብለዋል፡፡
የኤርትራው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዑስማን ሳሌህ ‹‹የህወሓት ቡድን እራሱን ለማስታጠቅ እና የአብይን መንግሥት ለማሽመድመድ የሚያደርጋቸውን ህገ-ወጥ እቅዶቹን ለመሸሸግ የተሳሳተመረጃ በማሰራጨት ላይ መሆኑን›› በመግለጽ የፀጥታው ምክር ቤት ‹‹ኢ-ፍትሐዊነትን ለማስተካከል ተገቢ እርምጃዎችን እንዲወስድ›› አሳስበዋል፡፡
ኡስማን ሳሌህ፣ የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በኤርትራ እና በኢትዮጵያ መንግስት እና ወታደራዊ ባለሥልጣናት ላይ የጣለውን የቪዛ እገዳም የተቹ ሲሆን፣ ውሳኔውን ‹‹በአንድ ወገን ብቻ የተፈፀመ የማስፈራራት እና ጣልቃ ገብነቶች›› የሚያሳይ የቅርብ ጊዜ ማሳያ እንደሆነ ገልጸዋል ሲል አል ዐይን አሶሼትድ ፕሬስን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል፡፡