አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ግንቦት 26፣ 2013 ― በኢትዮጵያ የአውሮፓ ኅብረት ጽሕፈት ቤት ቁልፍ የሰብዓዊ ረድኤት አጋሮቹ ጋር ለትግራይ ክልል የሚውል 500 ሚሊየን ዶላር ማዋጣታቸውን በማመልከት መንግሥት ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቋል፡፡
ጽሕፈት ቤቱ በትዊተር ገጹ ላይ እንዳሰፈረው በክልሉ ከፍተኛ ርሃብ እንዳይከሰት ለመታደግ አፋጣኝ ርምጃ መወሰድ እንዳለበት የጠየቀ ሲሆን፣ ለሲቪሎች ከለላ ማድረግና ሕይወት ማዳን እንደሚያስፈልግም ገልጿል።
ሁሉም ወገኖች ከኃይል ርምጃ እንዲታቀቡ፣ ለሰብዓዊ ርዳታ ያልተደናቀፈ አቅርቦት እንዲፈቅዱ እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ሕጎችን እንዲያከብሩም ጠይቋል።
በተመሳሳይ በአዲስ አበባ የሚገኙ የውጭ አገራት ኤምባሲዎች በትግራይ የተኩስ አቁም ጥሪ ማቅረባቸው መነገሩ የሚታወስ ነው፡፡ በትግራይ ክልል ሰብዓዊ ዕርዳታ ማቅረብ እንዲቻል ተኩስ አቁም መደረግ እንዳለበት የጠየቁት በአዲስ አበባ የሚገኙ የጀርመን፣ የዩናይትድ ኪንግደም፣ የአሜሪካ እና ፈረንሳይ ኢምባሲዎች ነበሩ፡፡