አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ግንቦት 24፣ 2013 ― ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ብሎ የሚጠራውና በመንግሥት ‹ሸኔ› የሚል ሥያሜ ያለው ቡድን የኤርትራ ጦር በተለያዩ የኦሮሚያ እና የቤንሻንጉል ጉሙዝ አካባቢዎች እንደሚገኙ ገልጧል፡፡
ቡድኑ ባወጣው መግለጫ ላይ እንዳስታወቀው በአሁኑ ወቅት የኤርትራ ጦር በኦሮሚያ ክልል ሆሮ ጉድሩ፣ ቄለም ወለጋ፣ ምዕራብ ወለጋ፣ ጉጂ እና በቦረና ይገኛል ያለ ሲሆን፣ በተመሳሳይ በቤንሻንጉል ጉሙዝ መተከል ዞን ይገኛል፡፡
ወታደሮቹ በሆሮ ጉድሩ ዞን 4ኛ በሚባል ካምፕ ውስጥ ይገኛሉ ያለው ቡድኑ፣ ልዩ ቦታው አባይ ጮመን ፊንጫ ስኳር ፋብሪካ እንደሆነም አስፍሯል፡፡
እነዚሁ የኤርትራ ጦር አባላት ወታደሮቹ በአካባቢዎቹ በንጹሐን ላይ ግድያ፣ ድብደባ፣ ዝርፊያ እና ሴቶችን መድፈራቸውን ቡድኑ አስታውቋል፡፡
‹የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት› የአፍሪካ ኅብረት እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኤርትራ ወታደሮች የኦሮሚያ ክልልን ለቀው እንዲወጡ ግፊት እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡
ጉዳዩን አስመልክቶ ከክልሎቹም ሆነ ከፌዴራል መንግስት በኩል እስካሁን የተሰጠ ምላሽ የለም፡፡