አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ግንቦት 21፣ 2013 ― ከሰሞኑ በሰሜን ሸዋ አካባቢ ከአማራ ከልል ኦሮሚያ ክልልን አቋርጠው ወደ አዲስ አበባ ለማግባት የሚንቀሳቀሱ ላይ ጥቃት ሲያደርሱ የነበሩ ታጣቂዎችን መደምሰሳቸውን የኦሮሚያ ክልል አስታውቋል፡፡
የክልሉ ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌታቸው ባልቻ ለሸገር እንደተናገሩት፣ አሊ ዶሮ በሚባል አካባቢ ታጣቂዎቹ አሽከርካሪዎችን በማስቆም ሲዘርፉ እና ጥቃት ሲፈፅሙ ነበሩ ያሉ ሲሆን፣ እነዚሁ ታጣቂዎችን የክልሉ የጸጥታ ኃይሎች የተወሰኑትን ሲይዙ ቀሪዎቹን ደምስሰዋል፡፡
ጥቃቱን የሚፈጽሙት የሸኔ አባላት ናቸው ያሉት የቢሮ ኃላፊው፣ በአሁኑ ወቅት ግን አጠቃላይ የክልሉ ሰላም የተሻለ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከሰሞኑ በሰሜን ሸዋ አካባቢ ታጣቂዎቹ ባደረሱት ጥቃት የቆሰሉ ሰዎች እንዲሁም የተቃጠሉ መኪኖችም መኖራቸው ነው የተነገረው፡፡