አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ግንቦት 18፣ 2013 ― ከሁለት ቀናት በፊት በፊት የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ላይ የቪዛ ማዕቀብ የጣለችው አሜሪካ እግዱን የምታጸና ከሆነ በአፀፋው የአሜሪካ ባለስልጣናት ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገቡ የሚያደርግ ተመሳሳይ እርምጃ እንደሚወሰድ አልጀዚራ ሥማቸው ያልተገለፀ የኢትዮጵያ ዲፕሎማትን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።
ኢትዮጵያ የምትጥለው የቪዛ እገዳው የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ብቻ የሚመለከት ሳይሆን፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የአሜሪካ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትንና ሰራተኞችን እንዲሁም በኢትዮጵያ ውስጥ ለሌሎች ድርጅቶች የሚሰሩ አሜሪካዊያኖችን እንደሚጨምርም ዲፕሎማቱ መግለጻቸው በዘገባው ተገልጿል።
ከዚህ በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር በመሆን ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ወደ ሶማሊያ የላከቻቸውን ወታደሮቿን ለመመለስ በጥናት ላይ መሆኗንና ከሶማሊያ በመቀጠል በመላው አፍሪካ ከአሜሪካ ጋር በተደረጉ ስምምነቶች ብቻ ሰላም ለማስከበር የላከቻቸውን ወታደሯቿን ትመልሳለች ማለታቸውም ተመላክቷል።