አምባ ዲጂታል፤ ሰኞ መጋቢት 18፣ 2015 – ድርቅ ባጠቃው የሶማሌ ክልሉ ዳዋ ዞን ለረዥም ጊዜ ጠፍቶ የነበረው ዝናብ መጣሉን ተከትሎ በተከተለ ጎርፍ የሰባት ሰዎች ሕይወት ተቀጥፏል፡፡
በዞኑ ጎርፍ ያስከተለው ኃይለኛ ዝናብ የጣለው ከመጋቢት 11 እስከ 14፣ 2015 ሲሆን፣ በዚሁ ሰበብ አራቱም የዞኑ አካባቢዎች በከባድ ጎርፍ ተጥለቅልቀው ከዚህ ቀደም በድርቅ ምክንያት በመጠለያ ጣቢያዎች የነበሩ በርካታ ሰዎች ጭምር ተፈናቅለዋል፡፡
አዲስ ስታንዳርድ የሁዴት የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር አስተባበሪ የሆኑት አቶ ሐሰን መሐመድን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ በጎርፉ የሞቱት ሰዎች ከቦጂ አራት፣ ከሂላል ቀበሌ አንድ፣ ከኤልጎፍ ቀበሌ አንድ እና ከሁዴት ቀበሌ 03 አንድ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡
በጎርፉ ከሞቱት ሰዎች በተጨማሪ እንስሳት ሲሞቱ፣ መኖሪያ ቤቶች እና የዞኑ አስተዳደር ጽሕፈት ቤቶችም ወድመዋል ነው የተባለው፡፡ ይኸው ጎርፍ ከ2 ሺሕ በላይ የሆነ የምግብ እህል አውድሟል፡፡