አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ የካቲት 8፣ 2014 ― የሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ቢሮ በማኅበራዊ ትስስር መድረኮች ላይ በክልሉ የመፈንቅለ መንግሥት ተደርጓል መባሉ ሐሰት መሆኑን እወቁት ብሏል፡፡
ቢሮው በአሁኑ ወቅት ጅግጅጋ ከተማን ጨምሮ መላው የሶማሌ ክልል እንደ ወትሮው ሁሉ ‹‹ሰላም እና መረጋጋት›› የሰፈነበት መሆኑን ገልጧል፡፡
አያይዞም በአንዳንድ ቦታዎች ‹‹ፀረ ለውጥ የሆኑ›› ያላቸው አካላት ‹‹በውጭ ሀገራት ከሚገኙ ለውጥ አደናቃፊ አካላት በድብቅ ግንኙነት ሲያደርጉ ተደርሶባቸው›› ከመንግስት መዋቅር የወጡ ሀይሎች ሰላም ለማደፍረስ ያደረጉት ሙከራ ‹‹ከህዝብ ጋር በመተባበር›› እንደከሸፈ አመልክቷል፡፡
የሶማሌ ክልል መንግሥት የህዝቡን ‹‹ሰላምን ለማደፍረስ›› ይንቀሳቀሳሉ ያላቸውን ኃይሎች እንደማይታገስና አስፈላጊውን ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ ነው የገለጸው፡፡
የሶማሌ ክልላዊ መንግሥት በተመሳሳይ ከአንድ ቀን በፊት ባወጣው መግለጫ በአሁኑ ጊዜ በክልሉ የተፈጠረውን ድርቅ ለፖለቲካ መጠቀሚያ የሚያደረጉትን እንደማይታገስ አስታውቆ ነበር፡፡
የክልሉ መንግስት መገለጫ የመጣው ከሳምምንት በፊት በሶማሌ ክልል የገዥው ብልጽግና ፓርቲ የተወሰኑ አመራርና አባላት በክልሉ ገዢ ፓርቲ የሆነው ፓርቲያቸው ውስጥ ተንሰራፍቷል ያሉትን የመልካም አስተዳደር ችግር ለመታገል የእርምት እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ከገለጹ በኋላ ነው፡፡
የቡድኑን መግለጫው በተመለከተ የተናገሩት የሶማሌ ብልጽግና ፓርቲ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መሐመዴ ሻሌ በበኩላቸው ግለሰቦቹ ከዚህ ቀደም በለውጡ ሰሞን ኃላፊነት ተሰጥቷቸው የነበረ ቢሆንም ከሥነ ምግባር ጋር በተያያዘ የተባረሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡