Sunday, October 6, 2024
spot_img

በፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የተተኩት የቀድሞው የትምህርት ሚኒስትር በጤና እክል ምክንያት እረፍት መጠየቃቸውን አሳወቁ

በትላንትናው እለት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ይፋ በተደረገው አዲሱ የመንግስት ካቢኔ በፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የተተኩት የቀድሞው የትምህርት ሚኒስትር ዶክተር ጌታሁን መኩሪያ በጤና እክል ምክንያት የሙሉ ጊዜ እረፍት መጠየቃቸውን አስታውቀዋል፡፡

የቀድሞው ሚኒስትር በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ማስታወሻ፣ ‹‹በጤንነቴ አሳሳቢነት የሙሉ ዕረፍት ጥያቄዬ ተቀባይነት በማግኘቱ ደስ ብሎኛል›› ብለዋል፡፡

በሥራ ባሳለፉባቸው ጊዜያት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በካቢኔያቸው እንዲያገለግሉ ለሰጧቸው እድል ያመሰገኑት ዶክተር ጌታሁን፣ ‹‹በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ጊዜ በ2008 ሚንስትር ዴኤታ እና በ2009 ሚንስትር ለመሆኔ አሻራዎ አለበት፤ አሁንም በጤንነት ችግር ሙሉ የእረፍት ጥያቄዬን ስለተቀበሉ በጣም አመሰግናለሁ›› ማለታቸውም ተመላክቷል፡፡

በትላንትናው ዕለት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በተካሄደው የካቢኔ አባላት ሹመት ላይ የትምህርት ሚኒስቴርን እንዲመሩ የተሾሙት ፕሮፌሰር ነጋ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

የተፎካካሪ ፓርቲ መሪው ፕሮፌሰር ነጋ በአሜሪካን አገር ከስቴት ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኒው ዮርክ በኢኮኖሚክስ ትምህርት ድግሪ ያገኙ ሲሆን፣ ኒው ስኩል ፎር ሶሻል ሪሰርች ከተሰኘው ተቋም ደግሞ የዶክትሬት ድግሪያቸውን በተመሳሳይ የትምህርት ዘርፍ ማግኘት የቻሉ ናቸው፡፡ በዚያው አገር ባክኔል ዩኒቨርሲቲን በመቀላቀል ኢኮኖሚክስ ትምህርት ያስተማሩት ብርሃኑ ነጋ፣ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማእረግ ያገኙት በ2007 ነበር፡፡ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ቀድሞ በተማሩበት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም ኤኮኖሚክስ ማስተማራቸው የሚታወቅ ነው፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img