Sunday, September 22, 2024
spot_img

የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ የመጣል ዕድሉ ዝቅተኛ እንደሆነ ተዘገበ

አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ መስከረም 22፣ 2014 ― የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጸጥታው ምክር ቤት በትግራይ እና የተመድ ኃላፊዎች ከኢትዮጵያ የመባረር ውሳኔ ላይ ትናንት በዝግ ተወያይቷል።

በምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ ቻይና እና ሩሲያ ጉዳዩን በዝርዝር ማጤን እንደሚያስፈልግ እና የትግራዩ ግጭት የውስጥ ጉዳይ መሆኑን በመግለጻቸው፣ ምክር ቤቱ ኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ የመጣል ዕድሉ ዝቅተኛ እንደሆነ ዲፕሎማቶችን ጠቅሶ ሬውተርስ ዘግቧል።

የዜና ወኪሉ የቻይና ልዑክ ቃል አቀባይ በተለይ የኢትዮጵያ መንግስት የተመድ ሠራተኞችን ለማባረር በመወሰኑ ላይ ተጨማሪ መረጃዎችን ማሰባሰብ እንደሚያስፈልግና በመንግስታቱ ድርጅት እና በመንግስት መካከል ጉዳዩ በንግግር እንዲፈታ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ነግረውኛል ብሏል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ትናንት በጀመረው የፈረንጆቹ ጥቅምት ወር የምትመራው ጎረቤት አገር ኬንያ ናት።

መንግስት ከትላንት በስትያ ሐሙስ መስከረም 20 በአስቸኳይ አገር ለቃችሁ ውጡ ያላቸው ሠራተኞችን ጉዳይ በተመለከተ የተመድ ዋና ጸሐፊ አንቶንዮ ጉቴሬዝ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ጋር በስልክ መነጋጋራቸው ተዘግቦ ነበር።

ጉቴሬዝ በዚሁ ወቅት የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የተመድ ሠራተኞችን የማባረር ሕጋዊ ሥልጣን የለውም የሚል መከራከሪያ ማቅረባቸው ተሰምቷል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለሠራተኞቹ መባረር ለትግራይ ሕዝብ የመጣ እርዳታ ለሕወሓት መስጠት፣ በፀጥታ ጉዳይ የተደረጉ ስምምነቶች መጣስ፣ የግንኙነት መሳሪያዎችን ለህወሀት መስጠት፣ የእርዳታ እህል ጭነው ትግራይ የገቡና ህወሀት ለወታደራዊ እንቅስቃሴ የሚጠቀምባቸውን 400 የሚደርሱ ተሽከርካሪዎችን ለመመለስ ተደጋጋሚ እንቅፋት መፍጠር እና የተሳሳተ መረጃ ማሰራጨታቸውን በምክንያትነት መጥቀሱም አይዘነጋም።

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img