አምባ ዲጂታል፣ እሑድ መስከረም 16፣ 2014 ― የብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ የሕዝብ ግንኙነቱ አቶ ታዬ ደንደዓ በኦሮሚያ ጨፌ ስብሰባ ላይ ያደረጉት ንግግር ውዝግብ ፈጥሯል።
አቶ ታዬ በጨፌው ከተመረጡት መካከል አንዳንዶቹን በሥም ጠቅሰው ሴክተር መስሪያ ቤትም እንኳን መርተው የማያውቁ ናቸው ሲሉ አብጠልጥለዋቸዋል።
የአቶ ታዬን ንግግር ተከትሎ በአዳራሹ የማጉረምረም ድምጾች ተሰምተዋል።
በመድረኩ አያይዘው እጩዎቹን በተመለከተ ያቀረባቸው ፓርቲው ነው ቢባልም እኔ ከአመራሮች መካከል ሆኜ አልሰማሁም ሲሉ የተደመጡት አቶ ታዬ፣ ፓርቲያችን የሚቀርበውን ነገር እንዴት አናውቅም፣ እንዴት ገሸሽ ሊያደርገን ቻለ ሲሉ ጥያቄ ሰንዝረዋል።
አቶ ታዬ ደንደኣ በኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ ስማቸው ከፊት ከሚጠራ መካከል መሆናቸውና ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ቅርበት ካላቸው የፓርቲው ሰዎችም የሚሰለፉ ስለመሆናቸው ይነገርላቸዋል።