አምባ ዲጂታል፣ ሰኞ መስከረም 10፣ 2014 ― የደቡብ ዞን የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ዋና አዛዥ ነበሩ የተባሉት ጎሌቻ ዴኒጌ ወደ ሰላማዊ ትግል መቀላቀላቸውን የመንግስት ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡
አቶ ጎሌቻ ከ14 ዓመት በላይ በደቡብ ዞን ግንባር የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎችን ሲመሩ መቆየታቸው የተነገረ ሲሆን፣ በዛሬዉ ዕለት የትጥቅ ትግል ትተዉ ለኦሮሞ ህዝብ ነፃነትና እኩልነት በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በተፈጠረው የዴሞክራሲና የሰላም አማራጭ ለመታገል ወስነዉ ተቀላቅለዋል ነው የተባለው፡፡
ጎሌቻ ዴኒጌ በመንግስት ሸኔ የሚባለውና ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ጦር ሲል የሚጠራው ቡድን በሽብርተኝነት ከተፈረጀው ሕወሃት ጋር የፈጠረውን ጥምረት በጫካ ውስጥ እያሉ ሲቃወሙ እንደነበር የተገለጸ ሲሆን፣ ኦሮሚያን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር ላይ የተካሄደዉ ምርጫ የኦሮሞ ህዝብ በነፃነት የተሳተፈበት ነበር ማለታቸውም በዘገባው ሠፍሯል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ሕዝቡ በመረጠዉ መንግስት መተዳደር ስላለበት የትጥቅ ትግል አያስፈልግም በሚል በዛሬው ዕለት ከነበሩበት ጫካ ወጥተው ከህብረተሰቡ ጋር መቀላቀላቸውንም ዘገባዎቹ አክለዋል፡፡