አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ነሐሴ 20፣ 2013 ― የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ላለው ችግር ጦርነት መፍትሔ እንደማይሆን ተናግረዋል፡፡
ኮሚሽነሩ በትግራይ ክልል ጦርነቱን ሸሽተው ወደ ሱዳን የተሰደዱ ሰዎችን በስደተኛ ጣቢያዎች አግኝተው ካናገሩ በኋላ በጣቢያዎቹ ያሉ ኢትዮጵያውያን ሰላም ከመጣ ወደ አገራቸው መመለስ እንደሚፈልጉ እንደነገሯቸው ገልጸዋል፡፡
መሬት ላይ ላለው ችግር ጦርነት መፍትሔ እንደማይሆን የገለጹት ፊሊፖ ግራንዲ፣ ሰላምን ለመመለስ ብቸኛው መፍትሔ ፖለቲካዊ ንግግር እና ድርድር መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡
በሱዳን መጠለያ ጣቢያዎች ያሉ ኢትዮጵያውያንን አስመልክቶም፣ የሚያገኟቸው አገልግሎቶች ቀድሞ ከነበረው መሻሻል እያሳዩ ስለመምጣቸውም አንስተዋል፡፡
በጥቅምት ወር መጨረሻ የተቀሰቀሰውን የፌዴራል መንግስት እና የሕወሓትን ጦርነት ተከትሎ በርካታ ሺሕዎች ወደ ጎረቤት አገር ሱዳን ተሰደው በመጠለያ ጣቢያዎች እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡