Sunday, September 22, 2024
spot_img

አብን የአማራ ወጣቶች ራሳቸውን ያስታጥቁ አለ

አምባ ዲጂታል፣ ማክሰኞ ሐምሌ 6፣ 2013 ― የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ‹‹የአማራ ህዝብ ከባድ ዋጋ ከፍሎ ያስወገደው የትህነግ ሀይል ዳግም እንዲያንሰራራና ህዝቡ በመስዋእትነት አስከብሮታል›› ያለውን ‹‹ማንነት በፖለቲካ አሻጥር እንዲገፈፍ የሚደረገው ጥረት ተቀባይነት የለውም›› በማለት የአማራ ወጣቶች ራሳቸውን እንዲያስታጥቁ ጥሪ አቅርቧል፡፡

ንቅናቄው ባወጣው መገለጫ ‹‹በአሁኑ ሰዓት የአማራ ህዝብ አፅመ ርስት ሆነዋል›› ያላቸው የኮረምና አላማጣ አካባቢዎች ‹‹በሕወሃት እጅ ስር እንዲወድቁ ግልፅ የሆነ የፖለቲካ አቋም የወሰደ መንግስታዊ ክፍል ስለመኖሩ የተረጋገጠ ጉዳይ ሆኗል›› ብሏል፡፡

ከመነሻው ህዝባችን የፖለቲካ ቁማር ማስያዥያ እንዳይሆን በሚል ያልተቋረጠ ጥሪ ስናቀርብ ቆይተናል ያለው አብን፣ ‹‹የተለያዩ አካላት በፈጠሩት ውዥንብርና የአመራር ክፍተት ምክንያት በአሁኑ ወቅት ዳግም ለህልውና አደጋ ተጋልጦ ይገኛል›› ሲል አመልክቷል፡፡

ሕወሃት በተቆጣጠራቸው አካባቢዎች በርካታ ሕዝብ ላይ ዘግናኝ ጭፍጨፋ መፈፀሙንም የጠቀሰው አብን፣ ይህ በመሆኑም መላው የአማራ ህዝብ ይህ ጉዳይ የታሪክና የማህበራዊ ክብር እንዲሁም የማንነት ጉዳይ መሆኑን በመረዳት አጠቃላይ ጥቃቱን ለመመከት አስቸኳይ ህዝባዊ ንቅናቄ እንዲያደርግ ጠሪ አቅርቧል፡፡

‹‹በሁሉም አካባቢዎች ያላችሁ የአማራ ፋኖዎች በአሁኑ ሰአት ሕዝብ ያጋጠመውን የህልውና ትግል ለመቀልበስ በግንባር ለመንቀሳቀስ ፈጣን ዝግጅት እንድታደርጉ››ም ያለ ሲሆን፣ ‹‹መላው የአማራ ህዝብ አካባቢውን ነቅቶ እንዲጠብቅና በተለይም በመካከላችን ሆነው ሴራና ጥቃት የሚያቀናብሩ፣ በሰርጎ ገብነት መረጃ ለጠላት የሚያቀብሉ አካላትን በንቃት በመከታተል የማክሸፍና የመቆጣጠር ስራ እንዲያከናውን›› ብሏል፡፡

አክሎም ‹‹በተለያየ የአመራር ጥፋትና ጥሰት ያላግባብ ተገፍታችሁ ከፀጥታና ከወታደራዊ አመራርነታችሁና ሙያችሁ ውጭ የተደረጋችሁ የአማራ ልጆች በሙሉ ህዝባችሁን ለመታደግ የሚደረገውን ታሪካዊ እንቅስቃሴ ለመቀላቀል ዝግጅት›› እንዲያርቡ ጠይቋል፡፡

ንቅናቄው በማሳረገያው ‹‹መላው የአማራ ህዝብ በዚህ አግባብ በፖለቲካ ሸፍጥና በአመራር ክፍተት ምክንያት የተደቀነብንን የህልውና አደጋ ለመቀልበስ ለሚደረገው ሁለንተናዊ ዘመቻ በትጥቅና ስንቅ አቅርቦት እንዲሁም በደጀንነት ርብርብ እንዲደረግ›› በማለት ጥሪ አቅርቧል፡፡

ተዛማጅ ጽሑፍ

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

ትኩስ ርዕስ

- Advertisment -spot_img