አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ሐምሌ 3፣ 2013 ― በትግራይ ክልል ለችግር ለተጋለጡ ወገኖች የሚውል ሰብዓዊ እርዳታ እየተጓጓዘ መሆኑ ተነግሯል፡፡
የእርዳታ ማጓጓዝ ሥራው የተጀመረው ዓለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶች በትግራይ ክልል ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች እርዳታ እንዲያቀርቡ ለመንግሥት ጥሪ ማቅረቡን ተከትሎ መሆኑ ነው የተሰማው፡፡
በዚሁ መሰረት ከ40 የሚበልጡ ከባድ የጭነት ተሽከርካሪዎች ከአፋር ክልል ሰመራ ከተማ የሰብዓዊ እርዳታ ጭነው ወደ ትግራይ ክልል መንቀሳቀስ መጀመራቸውን የመንግሥት ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡
ተሽከርካሪዎቹ ምግብ እና ምግብ ነክ ያልሆኑ እርዳታዎችን የጫኑ ሲሆን፣ የሰብዓዊ ዕርዳታው በትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ለተጎዱ ወገኖች ይሠራጫል ተብሏል፡፡