አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ሰኔ 30፣ 2013 ― የፌደራሉ መንግሥት የሰብዓዊ እርዳታ ማቅረብ ለሚሹ ሁሉም አካል ወደ ትግራይ በረራ እንዲያደርጉ መፍቀዱን በዛሬው እለት አስታውቋል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ መረጃ ማጣሪያ በትዊተር ገጹ ይፋ እንዳደረገው የፌደራሉ መንግሥት ወደ ትግራይ የሚደረጉ በረራዎችን ከትላንት በስትያ ሰኞ ሰኔ 28፣2013 ጀምሮ መፍቀዱን ይፋ አድርጓል፡፡
ሆኖም መንግሥት የሰጠው የበረራ ፍቃድ ከዓለም አቀፍ መነሻዎች በቀጥታ ወደ ትግራይ ለሚደረጉ የቀጥታ በረራዎች ይሁን አልያም በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ከሚገኙ የአየር ማረፊያዎች ወደ ትግራይ ክልል ስለሚደረጉ በረራዎች ስለመሆኑ ግልጽ የሆነ ነገር የለም።
የፌደራል መንግሥት ባለፈው ሳምንት ሰኞ የተናጠል የተኩስ አቁም ማወጁን ተከትሎ፣ የህወሓት ኃይሎች በተመሳሳይ የተኩስ አቁም ለማድረግ ባለ ሰባት ነጥብ ቅድመ ሁኔታዎችን ባለፈው እሑድ ለፌደራሉ መንግሥቱ ማቅረባቸው ይታወሳል።
ከእነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች መካከል ‹‹ያለ ቅድመ ሁኔታ ዓለም አቀፍ በረራዎች በትግራይ ወደሚገኙ አየር ማረፊያዎች የቀጥታ ጉዞ እንዲያደርጉ መፈቀድ›› የሚል የተካተተበት እንደነበር ይታወሳል፡፡