አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ሰኔ 26፣ 2013 ― ብልጽግና ፓርቲ በሰድስተኛው አገራዊ ምርጫ የሚያሸንፍ ከሆነ በምርጫ የተሳተፉ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደ ተሳትፏቸው ከዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ የመንግሥት መዋቅር ውስጥ ውክልና ወይም ተሳትፎ እንዲኖራቸው እንደሚያደርግ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገልጸዋል፡፡
የምርጫ ውጤቱ በተቃራኒ ሆኖ ብልጽግና ፓርቲ የሚሸነፍ ከሆነም፣ የኢትዮጵያን አሸናፊነት ለማረጋገጥ መንግሥት ለአሸናፊው የፖለቲካ ፓርቲ ሥልጣኑን በሰላማዊ መንገድ እንደሚያስረክብ ተናግረዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ያሉት የኢትዮጵያ ሲቪክ ማህበራት ድርጅቶች ምክር ቤት ‹‹ኢትዮጵያ አሸንፋለች እና እናመሰግናችኋለን›› በሚል ባዘጋጀው የምሥጋና ፕሮግራም ላይ ነው፡፡
በምርጫው እለት ዜጎች ኢትዮጵያ አሸናፊ እንድትሆን እስስ እኩለ ሌሊት ድረስ ወጥተው ድምጽ በመስጠታቸውም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምሥጋናቸውን አቅርበዋል።
አክለውም ኢትዮጵያዊያን ከፖለቲካ ይልቅ አገር ትቀድማለች የሚል መርህ አንግበው ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በማካሄድ አገራቸውን አሸናፊ አድርገዋልም ነው ያሉት።