አምባ ዲጂታል፣ ረቡዕ ሰኔ 23፣ 2013 ― የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፍልሰተኞች ኤጀንሲ እና የዓለም ጤና ድርጅት ከሰሞኑ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ለቆት የወጣው የትግራይ ክልል ለወረርሽኝ ስጋት እንዳይጋለጥ ስጋት እንደገባቸው አስታውቀዋል፡፡
የመንግሥታቱ ድርጅት የፍልሰተኞች ኤጀንሲ ቃል አቀባዩ ቦሪስ ቼሺኮቭ በጄኔቫ ጉዳዩን አስመልክቶ በተናገሩበት ወቅት፣ በተለይ በክልሉ መቀመጫ መቐለ ከተማ ያለው ሁኔታ እጅጉን አሳሳቢ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በክልሉ የመገናኛ ዘዴዎች መቋረጣቸውን ያመለከቱት ቃል አቀባዩ፣ ይህ መሆኑ በክልሉ የሰብአዊ አቅርቦት ላይ በሚሠሩ ባልደረቦቻው ላይ ሁኔታዎችን አስቸጋሪ አድርጓል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል የዓለም ጤና ድርጅት ቃል አቀባዩ ታሪክ ያሳሬቪች በበኩላቸው፣ በክልሉ የምግብ እጥረት፣ ንጹሕ ውሃ፣ መጠለያ እና በቂ ሕክምና አለመኖሩን አንስተው፣ ይኸው ሁኔታ ለተቅማጥ፣ ለኩፍን እና ወባ የተመቸ ስለሆነ ስጋት እንደገባቸው መግለጻቸውን አናዶሉ ኤጀንሲ ዘግቧል፡፡
በትግራይ ክልል ስምንት ወራት ባስቆጠረው የሕወሃት እና የፌዴራል መንግሥት ጦርነት ሰበብ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ቀያቸውን ለቀው መሰደዳቸው በተባበሩት መንግሥታት እና በሌሎችም የረድኤት ተቋማት መነገሩ የሚታወስ ነው፡፡