አምባ ዲጂታል፣ ቅዳሜ ሰኔ 19፣ 2013 ― በቻምፒዮን ኮሚኒኬሽንስ በየሳምንቱ ቅዳሜ ለኅትመት የሚበቃው ‹‹አዲስ ማለዳ›› ጋዜጣ፣ ከዛሬ አንስቶ በአፋን ኦሮሞ እና በሶማሊኛ ቋንቋ መረጃ ማቅረብ ጀምሯል፡፡
ጋዜጣው እንዳስታወቀው ሁለቱ የአገር ውስጥ ቋንቋዎች ከጋዜጣው አራት አራት ገጾች የተመደቡላቸው ሲሆን፣ ቀድሞ በሥርጭት ላይ ከሚገኘው የአማርኛው ኅትመት ጋር ባንድነት ተካተው ይቀርባሉ፡፡
በቋንቋዎቹ የሚቀርቡት ይዘቶች በአማርኛ ቋንቋ ከቀረቡ ዜናዎች እና አምዶች ተመርጠው የሚተረጎሙ እንደሚሆን ታውቋል፡፡
ጋዜጣው በቀጣይ በአጭር ጊዜ ውስጥ በኦሮሚያ እና ሶማሊ ከተሞች ዘጋቢዎች በቋሚነት በመቅጠር የሚዘግቡበትን ሁኔታ ለማመቻቸት እየሠራ እንደሚገኝና በጊዜ ሒደት በሁለቱም ቋንቋዎች የሚዘጋጁ ራሳቸውን የቻሉ ጋዜጦች እንዲኖሩ ለመድረግ እንደሚሠሩ የአሳታሚው ሥራ አስኪያጅ አቶ ታምራት አስታጥቄ ገልጸዋል፡፡
አዲስ ማለዳ ጋዜጣ በእንግሊዝ አፍ የሚታተመው ‹ኢትዮጵያን ቢዝነስ ሪቪው› መጽሔት እህት ኅትመት መሆኑ ይታወቃል፡፡