አምባ ዲጂታል፣ ዐርብ ሰኔ 11፣ 2013 ― የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአውሮፓ ኅብረት ልዩ መልእከተኛ በትላንትናው እለት በኅብረቱ ምክር ቤት ቀርበው ስለ ትግራይ የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ተናግረውታል ብለው ያቀረቡት ፍጹም ፈጠራ መሆኑን ባወጣው መግለጫ አሳውቋል፡፡
የኅብረቱ መልእክተኛ በንግግራቸው ‹‹ባለፈው የካቲት የኢትዮጵያ ባለስልጣናትን ባገኘኋቸው ጊዜ የትግራይን ሕዝብ እንደሚያጠፉት፣ እንደሚያወድሙትና 100 ዓመታት ወደ ኋላ እንደሚመልሱት ቃል በቃል ነግረውኛል› ሲሉ ተደምጠው ነበር፡፡
የፔካ ሐቪስቶን ንግግር ኃላፊነት የጎደለው ነው ያለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በዚሁ ሰበብ ኢትዮጵያ ከአውሮፓ ኅብረት ጋር ግንኙነትዋን ማጠናከር ብትፈልግም ከዚህ በኋላ ግን ግለሰቡን እንደ ተወካይ መቀበል ይቸግራታል ብሏል፡፡
ባለፉት ስድስት ወራት ለሁለት ጊዜያት ወደ አዲስ አበባ የመጡት ፔካ ሐቪስቶ፣ ፕሬዝዳንት ሳሕለወርቅ ዘውዴን ጨምሮ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ምክትላቸው ደመቀ መኮንን እንዲሁም የሰላም ሚኒስትሯ ሙፈሪሃት ካሚልን ማግኘታቸውን የውጭ ጉዳይ አስታውሷል፡፡
ብዙዎችን ያስደነገጠውን ንግግር ያደረጉት ፔካ ሀቪስቶ ያሉትን ጉዳይ ከማን እንደሰሙ የጠቀሱት ነገር የለም፡፡