አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ግንቦት 26፣ 2013 ― የዴንማርክ ፓርላማ በዛሬው ዕለት ጥገኝነት ጠያቂዎች ጉዳያቸው በሕጋዊ መንገድ እስኪያልቅ ከአውሮፓ አገራት ውጪ እንዲቆዩ የሚለውን ሕግ በ70 ድምጽ አጽድቋል።
መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እና የተመድ የስደተኞችን መብት ይጻረራል በሚል ዴንማርክ እንዳታጸድቅ ሲያሳስቡ የሰነበቱት ሕግ፣ ከአገሪቱ ምክር ቤት 24 ተቃውሞ ብቻ ነው የገጠመው።
ፀረ ስደተኞች አቋም ያራምዳል በመባል የሚተቹት የጠቅላይ ሚኒስትር ማቲ ፍሬዴሪክሰን ሶሻል ዴሞክራት መንግሥት ይህን ሕግ ያጸደቀው ስደተኞች ወደ ዴንማርክ እንዳይመጡ ለማገድ ነው ተብሏል።
በአዲሱ ሕግ መሰረት ስደተኞች የጥገኝነት ጥያቄያቸውን ዴንማርክ ድንበር ላይ በአካል ተገኝተው በማቀርብ የማመልከቻቸው ሂደት እስኪጠናቀቅ ከአውሮፓ ውጭ በሚገኝ የጥገኝነት ጠያቂዎች ማዕከል መቆየት ይጠበቅባቸዋል።
ጥያቄያቸው ተቀባይነት ካገኘ ብቻ ነው ወደ ዴንማርክ የመግባት መብት የሚሰጣቸው ሲሆን፣ ጥያቄው ተቀባይነት ያጣ ከሆነም በእንግድነት ከሚቆዩበት ሀገር እንዲወጡ ይጠየቃሉ።
ዴንማርክ ስደተኞቹን ከአውሮፓ ውጭ የማቆያ ማዕከል ታዘጋጃለች ተብሎ የሚገመተው በግብጽ፣ ኤርትራና ኢትዮጵያ ሊሆን እንደሚችል ቢነገርም ከሩዋንዳ ጋር በጉዳዩ ላይ መነጋገር መጀመሯን ዘገባዎች ጠቅሰዋል።
የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ጆሚሽን ዴንማርክ ይህን ሕግ እንዳታጸድቅ አጥብቆ አሳስቦ ነበር።
ዴንማርክ አውሮፓ ውስጥ ስደተኞችን አስመልክቶ እጅግ የከፋ አቋም ከሚያራምዱ ሃገራት አንዷ መሆኗን የአዣንስ ፍራንስ ፕረስ ዘገባ ያመለክታል፡፡