አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ግንቦት 26፣ 2013 ― የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በሚሠራው ሥራ ከሁሉም ብሔረሰቦች እና ከአንዳንድ የመንግሥት ባለሥልጣናት ወቀሳ እንደሚቀርብበት ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ ለዘ ጋርዲያን ጋዜጣ ገልጸዋል፡፡
እርሳቸው ሥልጣኑን ከያዙት ወዲህ ኮሚሽኑ በተለያዩ ጊዜያት ሪፖርቶችን እንዳወጣ ያስታወሱት ዶክተር ዳንኤል፣ የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች የሚመቻቸውን የኮሚሽኑን ሪፖርት ነጥለው በማራገብ የፖለቲካ አጀንዳቸውን እንደሚያራምዱበትም ጠቁመዋል።
ዶክተር ዳንኤል አንዳንድ የአመኔታ ችግሮች እንደሚነሱም የጠቀሱ ሲሆን፣ ይህ የመጣው በኢትዮጵያ የመንግሥት ተቋማት የገለልተኝነት ታሪክ ስለሚያንሳቸው መሆኑን አመልክተዋል፡፡
አሁን እርሳቸው የሚመሩት ኮሚሽንም ቀድሞ በገዢው ፓርቲ አባላት የተሞላ እንደነበር በመግለጽ፣ አሁን ግን በወህኒ ቤቶች ድንገተኛ ቅኝት ማድረግ እና የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በገለልተኛነት ማጣራቱ ከመንግሥት ተጽዕኖ ነጸ መሆኑን እንደሚያሳይም አስረድተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽንም ገለልተኛ ተደርጎ የመታሰብ ደረጃው ከፍ እያለ መምጣቱንም ዶክተር ዳንኤል አክለዋል፡፡