አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ግንቦት 26፣ 2013 ― የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በእስር ላይ የሚገኙት የባልደራስ ሊቀመንበር አቶ እስክንድር ነጋና ሌሎች ፍርድ ቤት የወሰነላቸው የፓርቲው አባላት በምርጫው እንዲሳተፉ እየሠራ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
የቦርዱ ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ይህንኑ በዛሬው እለት በችሎት ተገኝተው ያስረዱ ሲሆን፣ ምርጫ ቦርድ በዚሁ ሰበብ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ተጨማሪ ወጪ እንደሚያወጣም ገልጸዋል፡፡
ቦርዱ ተጨማሪው ወጪ ቀድሞ ታትመው የነበሩ የድምጽ መስጫ ወረቀቶችን በአዲ ለመተካት የሚያወጣው መሆኑ ነው የተነገረው፡፡ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ባሳለፍነው ሰኞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት እነ አቶ እስክንድር ነጋ በዕጩነት እንዲመዘገቡ የሰጠውን ውሳኔ ለምን መፈጸም እንዳልቻለ በፍርድ ቤት ቀርቦ ያስረዳ ሲል ትእዛዝ ሰጥቶ እንደነበር አይዘነጋም፡፡