አምባ ዲጂታል፣ ሐሙስ ግንቦት 19፣ 2013 ― ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ (ባልደራስ) በእስር ላይ የሚገኙት ሊቀመንበሩ እስክንድር ነጋን ጨምሮ በሰበር ሰሚ ችሎት ምርጫ እንዲወዳደሩ የተፈረደላቸው አባሎቹን ምርጫ ቦርድ ለመመዝገብ እቸገራለሁ ማለቱን ተከትሎ የፍርድ ቤት ውሳኔ እንዲፈጽምልኝ የአፈጻጸም ክስ እመሰርታለሁ ብሏል፡፡
የፓርቲው የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ጌታነህ ባልቻ ለሸገር እንደተናገሩት ቦርዱ ቀድሞም እነ እስክንድር ነጋን መከልከል እንዳልነበረበት የገለጹ ሲሆን፣ አሁንም ቢሆን አባሎቹን ተጨማሪ እጩ አድርጎ እንዲዛቸው ሳይሆን በምትክ እንዲይዛቸው መጠየቃቸውን አስረድተዋል፡፡
ይህን ማድረግ ከባድ ጉዳይ አለመሆኑን ያነሱት ኃላፊው፣ በጥቃቅን ምክንያቶች የታሳሪዎች መብት መሸርሸር እንደሌለባቸውም ገልጸዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ በፍርድ ቤት በምርቻ እንዲወዳደሩ የተወሰነላቸው የባልደራስ አባላትን በእጩነት ለመመዝገብ እቸገራለሁ ለማለቱ በምክንያትነት ያስቀመጠው፣ የእጩዎች ምዝገባ መጠናቀቁን፣ እንዲሁም እያንዳንዱ እጩ ተወዳዳሪ በድምጽ መስጫ ወረቀት ላይ የሚኖረው ሥፍራ የሚወስን እጣ በማውጣቱና በዚሁ መሠረት የድምጽ መስጫ ወረቀቶች ሕትመት ተጠናቆ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች መላኩ ተግባር በቅርብ ጊዜ የሚጀመር መሆኑን ነው፡፡