የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰኔ 14፣ 2013 ድምጽ የሚሰጥባቸው ቦታዎች የመራጮች ሂደቱ ያለምንም ችግር በተከናወነባቸው ቦታዎች ብቻ እንደሚሆኑ አሳውቋል።
እንደ ቦርዱ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ ሶልያና ሽመልስ ከሆነ በመራጮች ምዝገባ ወቅት አቤቱታ በቀረበባቸው በሶማሌ ክልል በሚገኙ ሰባት የምርጫ ክልሎች የድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ በሰኔ 14 አይከናወንም።
ቦርዱ በእነዚህ ሰባት የምርጫ ክልሎች ማጣራት እያደረገ መሆኑን የጠቆሙት ወይዘሪት ሶልያና፤ ማጣራቱን የሚያከናውኑ 10 ቡድኖች ወደ ሥፍራዎቹ መላኩን አስረድተዋል።
የመራጮች ምዝገባ እስካሁንም ባልተጀመረባቸው እና በርካታ ተፈናቃዮች ባሉባቸው ቦታዎች በሰኔ 14 ድምጽ እንደማይሰጥም የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊዋ አመልክተዋል።
በሁለቱም ምክንያቶች በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስር ባለው የመተከል ዞን በዕለቱ የድምጽ መስጫ ሂደቱ እንደማይደረግም ጠቁመዋል። በእነዚህ ቦታዎች የሚደረገው የድምጽ አሰጣጥ “አሁን ካለው ሰኔ 14 ውጭ የሚታይ ነው” ማለታቸውንም የኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘገባ ያመለክታል።